Breaking News
Home / Documents / The TPLF Manifesto

The TPLF Manifesto

መቅድም

ይህ መፅሔት የትግራይ ሕዝብ ሃቀኛ ወኪል የሆነው የትግራይ ሕዝብ ነፃ አውጪ ድረጅት (ተ.ኅ.ህ.ት) መግለጫና የትግሉ መመርያ ነው። የትግራይ ሕዝብ ማለት በትግራይ ውስጥ የሚኖሩትንና በተለያየ ምክንያት ከትግራይ መሬት ውጭ የሚኖሩትን ሕዝቦቿ በሙሉ ያጠቃለለ ነው። [ትግሮኛ ተናጋሪዎች፣ ኣፋር (ጠልጣል)፣ አገው፣ ሳሆ፣ ኩናማ፣ ወ.ዘ.ተ.] የትግራይ መሬት በደቡብ ኣለውና፣ በሰሜን መረብ ሲያካልሉት በምዕራብ በኩል ደግሞ ወልቃይትንና ፀለምትን ያጠቃልላል።

ትግራይ አክሱም እስከወደቀችበት ጊዜ ድረስ የአክሱም መንግሥት እየተባለች ትጠራ ነበር። ኣክሱም ከወደቀች በኋላም እራሷን በማስተዳደር ለብዙ ጊዜ ብትኖርም ቅሉ ኣልፎ ኣልፎ ባካባቢዋ ለነበሩት ነገሥታት ግብር መክፈሏ አልቀረም።

በኣፄ ዪሐንስ ዘመነ መንግስት ኃይሏ በርትቶ በአካባቢዋ የነበሩትን ነገሥታት በቁጥጥሯ ሥር አውላ ነበር፤ ይሁን እንጅ አፄ ዩሐንስ ከሞቱ በኋላ በዳግማዊ ምኒልክ ኣማካኝነት ትግራይ በሸዋው ማእከላዊ ግዛት ሥር ወደቀች። ከዚህ ጊዜ ሀኋላ ነው የአማራው የመሳፍንት ቡድንና ተከታዮቹ የትግራይን ነፃነት ገፈው የሕዝቧን አንድነት ያናጉት። ግልጽና ስውር በሆኑ ዘዴዎችም (ሸዋዊ ዘይቤዎች) የትግራይ ሕዝብ በድንቁርና፣ በበሽታ፣ በረሃብ አዘቅት ውስጥ እንዲሰምጥ ያደረጉት። በተለይም ትግሬነቱን በፍጥነት እንዲክድና ያለውድ በግድ “አማራ ለማድረግ” ያልሞከሩት ዘዴ ባይኖርም መሬቱ ተቆራርሶ ስለተወሰደበትና የተደራረበ ጭቆና ስለደረሰበት አገሩን ጥሎ ተሰደደ። ባጠቃላይ ባሁኑ ጊዜ ትግራይ ነፃነቷ የተገፈፈች፣ መሬቷ ተቆራርሶ የተወሰዳባትና የተወሳሰብ ችግር የደቆሰው ሕዝብ የሚኖርባት ጭቁን ብሔር ናት።

ተ.ሓ.ህ.ት. ግልጽ ፖልቲካዊ ማነቃቃትና ሰራዊታዊ ንቅናቄ በትግራይ ምድር ማካሄድ የጀመረበት ከየካቲት ወር 1967 ዓ.ም. ወዲህ ቢሆኑም ቅሉ ከዛ በፊት የብሔረ ትግራይ ተራማጆች ድረጅት (ብ.ት.ተ.ድ.) በሚል ስም ለስድስት ወራት ያህል ምስጢራዊ ድርጅታዊና ሰራዊታዊ መዘጋጅትን አድርጓል። ይሁን እንጂ ተ.ሓ.ህ.ት. በዚህ ጊዜ ብቻ የተፈጠረ ተዓምራታዊ ትግል ሳይሆን፦

ሀ. ጭቁኑ የትግራይ ሕዝብ ከሰማንያ (80) ዓመት ባላይ ትግል በኋላ ያፈራው ፍሬና፦

ለ. ተራማጅ ትግሬ ከ1962 ዓ.ም ጀምሮ ፀንሶት የነበረው አንጋፋ ልጅ ነው።

ሰፋ ያለ ትክክለኛ የትግራይን ታሪክ ለማወቅ “የትግራይ ታሪክ፣ መሬቷና ሕዝቦቿ” በሚል ርዕስ ተ.ሓ.ህ.ት. ያዘጋጀውን መጽሔት መመለክቱ ይጠቅማል።

መግቢያ

የመድብ ብዝበዛና ብሔራዊ ጭቆና በሰፈነበት ሥርዓት ንቁና ተረማጅ የሆኑ ሁሉ ከተጨቆነው ሰፊ ሕዝብ ጋር ሆነው ለተጨቆነው ሕዝብ ጥቅም ሲሉ ብሔራዊና ሕብረተሰባዊ ዓላማዎችን ያዘለ መሠረታዊ ለውጥ (አብዮት) የማካሄድ ትልቅ ኃላፊነት አለባቸው።

የተጨቆኑት ላብ-አደሮችና ድሀ ገበሬዎች የሚያሰቅቅ ኢኮኖሚያዊ ብዝበዛና ፓለቲካዊ ጭቆና ደርሶባቸው በተለያየ ዘዴ የተፋፋመ ትግል በሚያደርጉበት በአሁኑ ጊዜ ለጭቁኑ ሕዝብ የሚቆረቆሩ ተራማጆች ትግሉን የማፋፋምና አብዮታዊ መስመሩን የማስያዝ ታሪካዊ ግዳጅ አለባቸው። በዓለም አቀፍ ኢምፐሪያሊዝምና ፋሽስታዊ ወታደራዊ መንግሥት በማካሄድ ላይ ያለው ጠጋኝ ለውጥ ምክንያት ሊደርስ የቻለው የባሰ ጭቁና ሊጠፋ የሚችለው በተደጋገመ አብዮታዊ እንቅስቃሴ ብቻ ነው። ይሁን እንጂ የተደጋገመ አብዮታዊ እንቅስቃሴ ለማካሄድ ማርክሳዊ-ለኒናዊ በሆነ ርእዮተ-ዓለምና በማኦ ሴቱንግ አስተሳሰብ የሚመራ አብዮታዊ ድርጅት ያስፈልጋል።

በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የምርት ግንኙነት መደባዊ ብዝበዛ ከማስከተሉም በላይ የብሔሮች ጭቆና እንዲኖር አድርጓል። ስለዚህ ፈሽስታዊ ወታደራዊ መንግስት የሚያደርገው ንኡስ-ከበርቴያዊ ጠጋኝ ለውጥ ላለመቀበል፣ የብሔረ-ትግራይ ሕዝብ ነፃነት የሚገኘው በትጥቅ ትግል ብቻ መሆኑን በመገንዘብና ታሪካዊ ግዳጁን ለመፈጸም ተ.ሓ.ህ.ት. ተብሎ የሚጠራ ብሔራዊ አብዮታዊ ግንባር አቋቋመ። ይህም በብሔራዊ ዲሞክራሳዊ አብዮት (ኤን.ዲ.አር) ወይም በሕብረተሰባዊ አብዮት ጊዜ የሚካሄድ ሃቀኛ ብሔራዊ ትግል በመሠረቱ መደባዊ ትግል መሆኑን በማመን ነው።

ስለዚህ፦

ማርክሳዊ-ለኒናዊ ትክክለኛና ሳይንሳዊ የላብ-አደር ርእዮተ-ዓለም መሆኑን በማመንና በአሁኑ ጊዜ የሚካሄደው አብዮት ከግቡ ሊደርስ የሚችለው ይህንን መመሪያ በማድረግ ብቻ መሆኑን በመገንዘብ፦

ብሔራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎችን በማስተዋልና ለዓላማችን መቃናት አስፈላጊ መሆኑን በመገንዘብ ፀረ-ንኡስ ከበርቴያዊ የፋሽስትነት፣ ፀረ-ብሔራዊ ጭቆናና ፀረ-ኢምፐርያሊዝም የሆነ ፖለቲካዊ አቋም በመያዝ፦

ባገር ውስጥ በተደረገው ጠጋኝ ለውጥ ንኡስ-ከበርቴያዊ ፈሽስትነት ከዓለም-አቀፍ ኢምፐርያሊዝም ጋር በመሻረክ የነበረውን የብሔሮች ጭቆና ስላባባሰውና ጭቆናውም እንዲራዘም ማድረጉን በማስታወስ፦

የኢትዮጵያ ጭቁን ሕዝቦች እንደሌሎች ያለበለፀጉ ሃገሮች ሕዝቦች በዓለም-ዓቀፍ ኢምፐርያሊዘምና በየሀገሩ ባሉት አድሃሪያን (በኢትዮጵያ በንኡስ-ከበርቴያዊ ጠጋኝ ለውጥ ፋሽስትነት) የተበዘበዙና የተጨቆኑ መሆናቸውን በመገንዘብ፣ ጭቆናውን ብዝብዛው ሊጠፋ የሚችለው የላብ-አደሮችና የድሀ ገበሬዎች መደረጀት ተደራጅተውም ወዝ-አደሩ የግንባር ቀደምትነት ታሪካዊ ተልእኮውን በመያዝ የፖለቲካ ትግሉን አፋፉም ብሔራዊ ዲሞክራሲያዊ አብዮት በማካሄድ ብቻ ነው። ወዝ-አደሩንና ድሀ ገበሬውን ለማደራጀት በቅድሚያ ማርክሳዊ-ለኒናዊ የሆነ የፖለቲካ ማሕበር ማቋቋም የግድ ያስፈልጋል። ይህ የፖለቲካ ማሕበር በመላው ኢትዮጵያ የሚደረገውን የፖለቲካ ትግል በመምራት (ብሔራዊ የትጥቅ ትግል በማካሄድ ላይ ካሉት ብሔሮች በስተቀር) በአሁኑ ጊዜ የትጥቅ ትግል በማድረግ ላይ ካሉት ጭቁን ብሔሮች ትግል ጋር በመተባበር
ድልን አግኝቶ መደባዊ ብዝበዛና ብሔራዊ ጭቆና ለማጥፋት የዲሞክራሲና የሕብረተሰብአዊነት መሠረት ሲጥል ብቻ መሆኑን በመረዳት፦

ቢሆንም ባለንበት ዘመን የነበረውን የብሔሮች ቅራኔ እየተባባሰ በመሄዱ እነዚህ ብሔሮች ተባብረው ባንድነት እንዲታገሉ ማድረግ በጣም አስቸጋሪና የማይቻል ሆኖ ይገኛል። ይህ ብቻ ሳይሆን ብሔራዊ ስሜት (በተለይ በብሔረ-ትግራት) የመደብን ንቃት ሸፍኖት ይገኛል። ይህም ሊሆን የቻለው ጨቋኝኛ ተጨቋኝ ብሔሮች ለብዙ ዘመናት በሃይል ተባብረው እንዲኖሩ በመደረጋቸው የተጨቆኑት ብሔሮች ጭቆናውን ሊሸከሙት አልቻሉም፤ ከእንግዲህ ወዲያም ተገደው በህብረት መኖር የማይቻልና ተጨባጭ ሁኔታ የማይፈቅድላቸው ቢሆንም አሁን ባለው የህብረት መልክ የህብረት ትግል ለማድረግ ህልምና የትምክህተኞች ምኞት መሆኑን በመገንዘብ፦

በተጨማሪም ደግሞ የትግራይ ሕዝብ የተጨቆነና የተበዘበዘ በመሆኑ ለዲሞክራሲ ፀረ-ብሔራዊ ተፅዕኖ፣ ፀረ-ንኡስ-ከበርቴያዊ ጠጋኝ ለውጥ፣ እንደዚሁም ፀረ-ኢምፐርያሊዝም የሆነ አቋም በመያዝ ብሔራዊ የትጥቅ ትግል ለማካሄድ ዝግጁ መሆኑን በማመን ነው።

የትግሉ ይዞታ መደባዊ ትግል ሆኖ ባሕሪው ግን ብሔራዊ ዲሞክራሲያዊ አብዮት ያዘለ ነው። ይህ አብዮት የትግሉ መጨረሻ ሳይሆን ወደ ሕብረተሰባዊነት መሸጋገርያ ድልድይ ሆኖ ለሕብረተሰባዊነት የሚያስፈልጉትን ማቴሪያላዊ ሁኔታዎች እንዲሟሉ የሚደረግ አብዮት ነው። ትግሉም ከማንኛውም ተጽዕኖ ነፃ ሆኖ ከዓለም አቀፍና ከአገር ውስጥ ተራማጅ ድርጅቶች ጋር የሚተባበርና አብዮታዊ እንቅስቃስያቸውን የሚደግፍ መሆኑን እየገለጽን፦

የሕዝባችን ተቆርቋሪዎች እንደመሆናቸን መጠን በተ.ሓ.ህ.ት. ሥር ተደራጅተን የሕዝባችንን ትግል ለማነቃቃትና ታሪካዊ መስመሩን ለማስያዝ የትግላችንን ችቦ አቀጣጥለናል።

ተ.ሓ.ህ.ት.

የተ.ሓ.ህ.ት. የትግል መነሻ፣ ባሕሪውና ዓላማው የሚመለከት ተጨማሪ ማብራሪያ

I. አሁን ስላለው ሁኔታ

1. ፖለቲካዊ ሁኔታዎች

ሀ. ፖለቲካዊ ሥልጣን

ለረጅም ጊዜ በቆየው የባላባታዊና የኢምፐርያሊስቶች ሥርዓት ባስከተለው ፓለቲካዊ ጭቆናና ኢኮኖማዊ ብዝበዛ ምክንያት ጭቁን የኢትዮጵያ ሕዝቦት በየካቲት ወር 1966 ዓ.ም አብዮታዊ ሕዝባዊ እንቅስቃሴ በማካሄድ በተለያዩ የትግል ዘዴዎች (ሥራ በማቆም የተቃውሞ ሰልፍ ወ.ዘ.ተ. በምድረግ) የደረሰባቸውን ግፍና በደል በግልጽ አስታወቁ። ለተፈጠረው አብዮታዊ ሁኔታ መነሻ የሆነው የጊዜው ችግሮች በኤርትራ የተፈጠረው ፖልቲካዊና ወታደራዊ ሁኔታ እየከፋ መሄድ፣ በብዙ ቦታዎች የረኃብ መስፋፋትና በችግሩም ምክንያት የብዙ ሕዝቦች ሕይወት መጥፋት፣ የቤንዚን የዕቃዎችና የእህል ዋጋ መናር ሲሆኑ መሠራታዊ መነሻ ግን የመሬት ይዞታው ሥር ዓትና የመንግሥት የኢኮኖሚ ውድቀት እንደዚሁም የመደቦች ቅራኔ መክረርና መሠረታዊ የሆኑት ዲሞክራሲያዊ መብቶች ለህዝቡ መነፈግ ነበሩ። እንቅስቃሴው አቋሙ ፀረ-ባላባታዊ ሥርዓትና ፀረ-ኢምፐርያሊዝም ሆኖ ለዲሞክራሲ ለሕብረተሰብ ፍትሕና ለኢኮኖሚያዊ ግስጋሴ የቆመ ነበር።

ጭቁን መደቦች በበለጠ ለመታገል በቀረቡበትና በተነቃቁበት በዚሁ እንቅስቃሴ ውስጥ የንእስ ከበርቴው መደብ ግንባር ቀደም ፖለቲካዊ ተሳትፎ ነበረው። የእንቅስቃሴው መልክ ከበርቴያዊ መስሎ በትግሉ ስልትና ሕዝባዊ ጥያቄዎች ግን የብሔራዊ ዲሞክራሲያዊ አብዮት ባሕሪይ ይዞ ነበር። ይሁን እንጂ ይህ እንቅስቅሴ ከነበረው ሁናቴ ጋር የተያያዙ ሁለት አብይት ጉድለቶች ነበሩት።

፩ኛ. የፖለቲካ ድርጅቶች አለመኖር

በማንኛውም አብዮት እንደታየው ጭቁን ሕዝቦች በሚገባ ታግለው ለማሸነፍ በመጀመሪያ መደራጀት አለባቸው። ጭቁን የኢትዮጵያ ሕዝቦች ግን ምንም አንኳን በጀግንነት ፀረ-ባላባታዊ ሥርዓትና ፀረ-ኢምፐርያሊዝም በሆነ መስመር ቢታገሉም ትግላቸው ከግቡ ለማድረስ ፖለቲካዊ መመሪያና ትክክለኛ የትግሉ መስመር እንዲከተሉ የሚያደርግ አብዮታዊ ድርጅት አልነበራቸው። ያለ አብዮታዊ ድርጅት ደግሞ አብዮታዊ ትግል ተካሂዶ ከግቡ እንደማይደርስ የታወቀ ነው።

፪ኛ. የመስፍናዊ ቡድኖች መተናኮልና የንጉሡ ቃል

በዚህ ጊዜ ሕዝባዊው ትግል አደናቅፎ የጭቁኑ ሕዝብ መደባዊ ጥቅም ጠባቂ በመምሰል የተነሳሳ አንድ መስፍናዊ ቡድን ተቋቋሙ። ቡደኑ ከወታደራዊ ባለሥልጣኖች ጋር የመንግሥት ሥልጣን ለመካፈል ከንጉሡ ጋር ተስማምቶ … ስምምነቱ ብዙ ተስፋዎች ባዘለ መንገድ በንጉሡ ቃል ተደግፎ በአዋጅ ለሕዝብ ተነገረ። ይህም የሕዝቡን መነሳሳት ለጊዜው እንዲበርድ አደረገው።

ይህ በዚህ እንዳለ ሕዝባዊውን እንቅስቅሴ “በሰላማዊ መንገድ እመራዋለሁ” ባይ “የምርጥ መኰንኖች” ደርግ ተቋቋመ። ደርጉ ሕዝቡን በማደናገር ለሕዝቡ የቆመ መስሎ ባዶ የተስፋ ቃል በመስጠት ቀስ በቀስ በጭቁን የኢትዮጵያ ሕዝቦች ስም የፓለቲካውን ሥልጣን ጨበጠ። ደርጉ የፖለቲካ ሥልጣኑን የያዘው ሕዝቡ ማንኛውም ዓይነት ጭቆና ባስመረረው ጊዜ ስለሆነ በአብዮታዊያንና በፀረ-አብዮታዊያን መካከል ትግል በግልጽ ተጀመረ።

የምርጥ መኰነኖቹ መንግሥት ፀረ-አብዮታዊ በመሆኑ ባዶ ተስፋዎችን እየሰጠ ፋሽስታዊ አዋጃጆችን አውጆ ዲሞክራሲያዊ ጥያቄዎችን እየረገጠ እንዲሁም አድሃሪ ምሁራንን ወጣት መሳፍንትንም ሳይቀሩ ሥልጣን እየሰጠ ከጊዜ ወደ ጊዜ ፋሽስታዊ ጠባዮን እያጋለጠ ሄደ።

ፋሽስታዊ ጠባዩን ለመሸፈን ሕዝቡን አታሎ የህዝቡን ትግል ለማደናቀፍ ህብረተሰብዓዊነት መመሪያው አስመስሎ “ህብረተሰባዊ” አዋጆች የመሬት ይዞታና ትርፍ ቤቶችን በሚመለከት ጉዳይ አወጣ። ይህ ያልንበት ምክንያት አዋጆቹ ሥራ ላይ ለማዋል በቅድሚያ መሟላት የሚገባቸው ነገሮች በመኖራቸውና የአዋጁ መንፈሰ አብዮታዊ መንገድ የተከተለ ሳይሆን የሕዝቡን ተቃውሞና የራስ የኢኮኖሚ ውድቀት ለመወጣት የተጠነሰሱ ፖለቲካዊ ሴራ በመሆኑ ነው። ይህ ብቻ ሳይሆን በደርጉ ውስጥ በቡድን የመከፋፈልና በስልጣን ሽሚያ መተናኮል መኖሩን ግልጽ እየሆነ መጣ። በቡድኖቹ መካከል ያለው ቅራኔና የሥልጣን ሽሚያ አሁንም መኖሩ ግልጽ ነው። ፋሽስታዊ ደረግ እድሃሪያንና ተራማጆችን እያሰረ አንድ ዓይነት ወንጀል የሠሩ ሊያስመስል ለሁሉም አንድ ዓይነት ፍርድ በመስጠቱ በዓለም ተወዳዳሪ የሌለው ፋሽስት መሆኑን አስመስክሯል።

ለ. የፖለቲካ ነፃነት አለመኖር

በህብረተስ ውስጥ መደቦች እስካሉ ድረስ ሃቀኛና ትክክለኛ የሆነ ነፃነትና እኩልነት ሲኖር አንደማይችል አያጠራጥርም። ይሁን እንጅ ጭቁን ሕዝቦች አብዮታዊ ትግላቸውን ለማካሄድ ሁኔታው የሚፈቅድላቸው የፖለቲካ ነፃነት ማለት የመናገር፣ የመጻፍ፣ የመሰብሰብ፣ የተቃውሞ ሰልፍ ማድረግና የመደራጀት መብት ሊሰጣቸው ይገባል።

እነዚህ መብቶች ለሕዝቡ መስጠት የሚችለው በሕዝቡ ለሕዝቡ የቆመ የዲሞክራሲያዊ ሪፖብሊክ መንግሥት ብቻ ነው። ለዚህ ነው የኢትዮጵያ ሕዝቦች ተራማጅ ወገኖች ፋሽስታዊውን ደርግ ለመጣል በሚያደርጉት ትግል ወደ ዲሞክራሲያዊ መንግሥት የሚያሸጋግራቸውን ጊዚያዊ ሕዝባዊ መንግሥት እንዲቋቋም ደጋግመው የሚጠይቁት። ይህ ጥያቄ ምንም እንኳ ጠንካራ ትግልና ረጅም ጉዞ የሚያስፈልገው ቢሆንም ታሪካዊ ጥያቄ ነው። ምክንያቱም ጭቁን ሕዝቦች ሳይደራጁ ቀርተው የፖለቲካ ሥልጣን ለመያዝ በማይችሉበት ጊዜ ጊዜያዊ አብዮታዊ መንግሥት በማቋቋም ሥልጣን ወደ ሌሎች አድሃርያን መደቦች ወይም ቡድኖች እንዳይተላለፍ ሊከላከሉ ይችላል።

በ1905 ዓ.ም እ.ኤ.አ. በሩሲያ የተደረገው ዲሞክራሲያዊ አብዮት ምሳሌ ብንወስድ በዚያን ጊዜ በሩሲያ ውስጥ የነበረው ተራማጅ የፖለቲካ ድርጅት የሰጠው ቀጥሎ ያለውን የፖለቲካ መመሪያ መረጃ ሊሆነን ይችላል።

መመሪያውም:-

“የላብ-አደሩን ጥቅም ለማስገኘትና ለህብረተሰባዊ አብዮት በቂ የሆነ የፖለቲካ ነፃነት ስለሚያስፈልገው፤ ለዚህም አምባገነናዊ መንግሥት በዲሞክራሲያዊ መንግሥት መለወጥ ስለሚያስፈልግ፤ ይህ ለማድረግ የሚቻለው ደግሞ ህዝባዊ እንቅስቃሴ አሸንፎ ጊዚያዊ አብዮታዊ መንግሥት ከተቋቋመ በኋላ መንግሥቱ በጊዜው ህዝባዊ ምርጫ እንዲካሄድ በማድረግ የአብዮቱ አካሄድና የጊዚያዊ አብዩታዊ መንግሥት አስፈላጊነት በመመልከት ጉዳይ ለሕዝቡ በቂ ገለጻ ማድረግ አስፈላጊ ነው። መንግሥቱ የላብ-አደሩ መደብ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ጥያቄዎች በቅድሚያ ሥራ ላይ እንዲውሉ ያደርጋል።” ይላል።

ይህ ጊዜያዊ አብዮታዊ መንግሥት ለኢትዮጵያ ጭቁን ህዝቦች ቢነፈግም ጥያቄው አሁንም መልስ ያላገኘ የጊዜው መፎክር ሆኖ ቀርቷል።

ሐ. ብሔራዊ ተፅዕኖ፦

በህብረተሰባዊነት ርእዮተ-ዓለም የብሔሮች ጥያቄ በሚከተለው መንገድ ይፋታል።

“የብሔሮች የራስ ዕድል ራስ መወሰን ማለት ተጨቋኝ ብሔር ከጨቋኝዋ ብሔር የፖለቲካ መገንጠል አድርጋ ነፃ የሆነ የራሷ መንግስት ማቋቋም ማለት ነው። የራስን ዕድል ራስ የመወሰን መብት የሚፈልጉትን መገንጠልን ያበረታታሉ። ብሎ መኰነን የመፋታት መብት የሚደግፉትን ቤተሰባዊ አንድነት ያላላሉ ብሎ እንደ መወንጀል የሚቆጠር የማጭበርብሪያና የሞኝነት አነጋግር ነው። ከዕለታዊ ተግባራቸው ጭቁን ህዝቦች የጂኦግራፊና የኢኮኖሚ መተሳሰር፣ የሰፊ አገር ሰፊ ገቢያ ጥቅም በሚገባ ያውቁታል። ስለዚህ ወደ መገንጠል የሚያመሩት ብሄራዊ ተፅዕኖ ባስከተለው የብሄሮች ቅራኔ ምክንያት በአንድነት መኖር በጭራሽ የማይቻል ሲሆን ወይም ሆኖ ሲገኝና የኢኮኖሚ መተሳሰር እንቅፋት ስለሚሆን ወይም ሆኖ ሲገኝ ብቻ ነው። በዚህ ጊዜ የከበርቴዎች አንድነትና የመደቦች ትግል ነፃነት በበለጠ ሊካሄደ የሚችለው በመገንጠል ብቻ ነው። የራስን ዕድል ራስን የመወሰን መብት መንፈግ ማለት የጨቋኝዋ ብሄር ጥቅም መጠበቅ ማለት ነው።”
ሌኒን

በተጨማሪም ሌኒን የመገንጠል አስፈላጊነት ሲገልጽ፦

“የሕብረተሰብ በመደብ መከፋፈል ለማጥፋት የተጨቋኙ መደብ አምባገነንነትን እንደሚያስፈልግ ሁሉ የማይቀረው የብሔሮች መዋሃድ ሊገኝ የሚችለው መሸጋገሪያ በሆነው የብሔሮች ነፃነት፦ ማለት የብሔሮች መገንጠል መብት ሙሉ በሙሉ ሲኖር ብቻ ነው።” ይላል።

እንግዲያውስ በዚህ መልክ የአማራ ብሔር በትግራይ ሕዝብ ላይ የምታደረገው ተፅዕኖ እንመልከት፤ በኢትዮጵያ ያሉት ጭቁን ብሄሮች በተለይ ብሄረ-ትግራይ በጨቋኝዋ ያማራ ብሄር የሚደረስባቸው ተፅዕኖ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጐላና እየተባባሰ በመሄዱ በብሄሮች መካከል አለመስማማትና መጠራጠርን አስከትለዋል። ይህ በመሆኑ የኢትዮጵያ ጭቁን ሕዝቦች በሙሉ በአንድነት ሆነው መደባዊ ትግልን ለማካሄድ ከማይችሉበት ደረጃ ደርሷል። በተለይ በየጊዜው እየከረረና እየተባባሰ በመሄድ ላይ ባለው የብሄሮች ቅራኔ ምክንያት የጨቋኝና የተጨቋን ብሄሮች ሶሻሊስቶች በዚህ ጉዳይ ላይ አስፈላጊ የሆነ ውይይት፣ መረዳዳት፣ ሃቀኛና ጠንካራ የሆነ አንድ ዓይነት አቋም ሊይዙ አልቻሉም። ይህ ሊሆን የቻለው የብሄረ አማራ ሶሻሊስቶች ትምክህተኞችና አድርባዮች ሆነው ስለሚገኙ ነው። በተራማጆ መካከልና በጭቁን ህዝቦች መካከል ያለው መለያየት ለመንግሥቱ ጥሩ አጋጣሚ ሆኖለት እድሜውን እንዲያራዝም ረድቶታል። ስለዚህ ጭቁን ብሄሮች ከብሔራዊ ተፅዕኖና ከማንኛውም ዓይነት ብዝበዛ ነፃ ለመውጣት መደባዊ መልክ ያለው ብሔራዊ የትጥቅ ትግል ማድረግ ሃቀኛና ትክክለኛ ሆኖ እናገኘዋለን። ብሔረ-ትግራይም ጭቁን ብሔር በመሆንዋ ከላይ የተገለጸውን የአርነት መንገድ መርጣለች።

መ. ፕሮፖጋንዳ፦

ተስፋ ብቻ ያዘሉ ፍሬቢስ ባዶ አዋጆችና መገለጫዎች በየጊዜው ይለፈፋሉ። እነዚህ ከእውነት የራቁ መግለጫዎችና ጽህፎች በመገናኛ መስመሮች በጭቁን ህዝብና በሀገር ስም ይታወጃሉ። የአዋጆቹ ዓላማ የህዝቡን አስተሳሰብ ለማደናገርና ወታደራዊ ደርግ በሥልጣን ላይ ለመቆየት ያለው ፍላጐት እንደዚሁም ቡድናዊ ጥቅም ለመጠበቅ ሆነ ተብሎ የሚደረግ የፖለቲካ ፕሮፓጋንዳ ነው። ፋሽስታዊው መንግሥት የኢኮኖም ውድቀት ሲያጋጥመው ችግሩን ለመወጣት ፋብሪካዎችን ኩባንያዎችንና የከተማ ቦታዎችን እንደዚሁም ባንኮችን በቁጥጥሩ ሥር የሚያደርግ አዋጅ አወጀ። በኤርትራ ውስጥ በሚደረገው ጦርነትና በኢትዮጵያ ውስጥ ሕዝባዊ እንቅስቃሴ ምክንያት ደርጉ ፋሽስታዊ ተገባሩን ለማካሄድ ገንዘብ ሲያጥረው የግብር አዋጅና የሕዝብን ንብረት በቁጥጥሩ ሥር አድርጓል። ከዚህም በላይ የሕዝቡ ፖለቲካዊ ተቃውሞ በርትቶ መንግሥቱን ሲያናገው ፋሽስታዊ አዋጆችን ያውጃል። በተጨማሪም የህዝቡ ተቃውሞ ጠንክሮ የመንግሥቱ አቋም በሚዳከምበት ጊዜ ሕዝቡን ለማታገል እንዳንድ መደለያ አዋጆችን ያውጃል። ፋሽስታዊ ጠባዩ እየተጋለጠ በሄድ ቁጥር ይህንን ጠባዩ ለመሸፈን በግብር ሊገለፅ የማይችል የወረቀት አዋጅ ያውጃል። ይሁን እንጅ ምንም አንኳን እነዚህ ባዶ ፕሮፖጋንዳዎች ለጊዜው የህዝቡን አስተሳሰብ ሊጠመዝዙ ቢችሉም በመጨረሻ የደርጉ ፋሽስትነትና አድሃሪነት ጠባዮ መገለጹ አልቀረም።

ቅጣት፦ ተራማጆችንና አድሃሪዎችን አንድ ዓይነት ክስ እንዲቀርብባቸው በማድረግ አንድ አይነት ፍርድ እንዲቀበሉ ተደርጓል። በተጨማሪም “ተራማጅ” አዋጆችን ተቃውማችኋል በሚል ርካሽ ምክንያት ተረማጆችን ለማጥፋት ፋሽስታዊው ደርግ የሚያደርገው ፀረ-አብዮታዊ ድርጊት ለማንም ግልጽ ነው። ይህም ምንም እንኳ የሕዝቡን የህሊና ፍርድ ለጊዜው ቢያወናብድም ውሎ አድሮ እውነቱ መገለጹ አልቀረም። የውሸት ፕሮፖጋንዳ የህዝቡን አስተያየት ለብዙ ጊዜ እወናብዶ እንደማይኖር የታወቀ ነው። እንዲያውን የደርጉ አድሃሪ ጠባዮ በይበልጥ እየተገለጠ ሂደዋል።

2. ኢኮኖሚያዊ ሁኔታዎች

ሀ. የመሬት ይዞታው ሥርዓትና ችግሩ

በትግራይ ውስጥ የመሬት ይዞታው ሥርዓት አብዛኛው መስፍናዊ ርስት ነው። ርስት በቤተሰብ ይዞታ የሚካሄድ ትውልድ ቆጥሮ ማረስ የሚያስችል የመሬት ይዞታ ሥርዓት ስለሆነ በዚህ መንገድ የጋራ ይዞታ ነው ለማለት ይቻላል። ከጠቅላላው ህዝብ ዘጠና ከመቶ የሚሆነው ዕለታዊ ተግባሩ ሙሉ በሙሉ በርሻ ላይ የተመሠረተ ስለሆነ መሬቱ ተከፋፍሎና ተቆራርሶ ይገኛል። እንደዚሁም የግል መሬትና ጉልት አለ። ይህ ቅጥ ያጣ ችግር መፍትሄ እንዲያገኝ መጀመሪያ መረዳት የሚያስፈልግ ነገር አለ። ይህም በትግራይ ውስጥ መሬት አርሶ ለመኖር ብቻ ሳይሆን በይበልጥ የተወላጅነት ምልክት ስለሆነ በህብረተሰቡ ውስጥ ያለው ዋጋ ከፍ ያለ መሆኑን ነው። ስለዚህ የመሬቱ ይዞታው ሥርዓት ለመለወጥ እርምጃ ከመወሰዱ በፊት የመሬት ይዞታ ለውጥ የሚያስፈልግ መሆኑን ማስተማርና ማስረዳት በቅድሚያ መደረግ ካለባቸው አብይት ጉዳዮች አንዱ ነው። እንደዚሁም የገበሬዎች የፖለቲካ ንቃት እንዲኖራቸው የመደብ ጠላታቸውን ተባብረው እንዲመክቱ ማደራጀት ያስፈልጋል።
በተጨማሪም በከተማና በገጠር ያለው የሥራ እጦት ችግር ለማቃለል የገጠር እንዱስትሪዎችን ማስፋፋይ ለርሻ መሳሪያዎችን መግዣና ማስፋፊያ መንግሥት የገንዘብና ማቴርያል እርዳታ ማቅረብ በቅድሚያ ሊፈጸሙ የሚገባቸው ሥራዎች ናቸው። ከዚህ በላይ የተጠቀሱት ተቀዳሚ ነገሮች ሳይፈጸሙ ማንኛውም አዋጅ መፍትሔ ሊሆን አይችልም። ደርጉ እነዚህን ነገሮች ሳያሟላ በአዋጅ ሃይል ለመጠቀም በመፈለጉ የነበረው ችግር እንዲባባስ አድርጎታል። ይህ ተግባር ጊዜውን ያልተከተለና ደርጉ ፋሽስታዊ ጠባዩን ለመሸፈን ሆን ብሎ ያደረገው ነው። ስለዚህ የደረጉ መንግሥት መንኮታኮትና ሥልጣን ወደ ህዝብ ማስተላለፍ የግድ አስፈላጊ ተግባር ሆኖ ይገኛል።

ለ. የእንዱስትሪዎች አለመስፋፋት

ትግራይ ጭቁን ብሄር በመሆንዋ በመንግሥት የተደገፈ ወይም በግል የተያዘ ኢንዱስትሪ ወይም ፋብሪካ ሊኖራት አልቻለም። እንዲስትሪዎች አዲስ አበባ ውስጥ (የጨቋንዋ ብሔር ዋና ከተማ) ተከማችተው ይገኛሉ።

በዚህ ምክንያት የከተሞችን አለመስፋፋትና የላብ-አደሮችን ቅጥር ማነስ በጉልህ ይታያል። የኢኮኖሚ እድገትና የህብረተሰቡ ንቃት ከፍ እንዳይል አድርጎታል። ለኢንዱስትሪዎች አለመስፋፋት ምክንያት የሆነው የመንግስት መመሪያ አድላዊ ስለሆነ ነው። የትግራይ ህዝብ ከሚያገኘው አነስተኛ ገቢ ከፍተኛ ግብር ቢከፍልም ለኢንዱስትሪዎች ማስፋፋያ የተደረገለት የመንግሥት ድጋፍ የለም። ባላባታዊ የሆነው የምሬት ይዞታ ሥርዓትም ለኢንዱስትሪዎች አለመስፋፋት አንዱ ምክንያት ነው። በተጨማሪም ፋሽስታዊ መንግስት ሥልጣን ላይ ለመቆየት ብዙ ገንዘብ ለወታደሮቹ ወጭ ስላስፈለገው ከትግራይ ህዝብ ብዙ ገንዘብ በግልጽም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ገፏል፤ በመግፈፈፍም ላይ ነው።

3. ሕብረተሰባዊ ሁኔታዎች

ሀ. ራስን መጣል (ዲ-ሁማናይዜሽን)

ከቀን ወደ ቀን እየተባባሰ የሚሄደው የኢኮኖሚ ብዝበዛ በሰፊው የትግራይ ህዝብ ላይ ድሕነት፣ ረኃብና ውርደት እየተደጋገመ እንዲደርስ አድርጓል። በተጨማሪም የትግራይ ህዝብ ለረጅም ዘመን ሰብዓዊና ፖለቲካዊ መብቱ ተነፍጎ ሲጠላና ሲናቅ እንዲሁም አድልዎ ሲፈጸምበት ቆይቷል። ይህም በደል ጨቋኝዋ የአማራ ብሔር ሆነ ብላ እንደመንግሥት መመሪያዋ አድርጋ ስትሰራበት የቆየች ሲሆን ፋሽስታዊ ደርግም በባሰና በመረረ መንገድ ቀጥሎበታል። ከዚህም የተነሳ ሰፊው የትግራይ ሕዝብ ኑኖው እንዲቆረቁዝ ተደርጓል። በዚህ ምክንያት የሥራ ማጣት ችግር፣ ሽርሙጥናና ስደትን ከማስከተሉም በላይ ራስን መጣልና መንከራተት የትግራይ ሕዝብ ዕለታዊ ተግባሩ ሆኖ ይገኛል። ስለሆነም ሕዝቡ ተጠርጣሪና የተጠላ እንዲሆን በመደረጉ በህብረት መኖር የማይችል ሆኖ ይገኛል።

ለ. የህበረተሰቡ ወደ ኋላ መቅረትና ዕረፍት ማጣት፦

ሰፊው የትግራይ ህዝብ ሥራ አጥቶ በሸሙጥናና በስደት ወ.ዘ.ተ. ብቻ ሳይሆን በረኃብ፣ በድንቁርናና በበሽታ እየተሰቃየ ይኖራል። እነዚህም ችግሮች ወንጀል እንዲፈጽም ይገፋፉታል። ለችግሩ መሠረታዊ ምክንያት ኢምፐርያሊዝምና ባላባታዊ ሥራዓቱ ይሁኑ እንጅ ጨቋኛዋ የአማራ ብሄር የምታደርገው የኢኮኖሚ ብዝበዛና የፖለቲካ ጭቆና ታክሎበት ነው። ከዚህም በላይ የሚያኮራው የህዝባችን ታሪክ፣ ባህልና ቋንቋ እንዲደክምና ተዳክሞ እንዲጠፋ ወይም የአማራ ብሔር የገዥ መደብ ጥቅም እንዲጠበቅ የ፫ ሺ ዓመታት ታሪክና ባህላችን መመኪያቸውና መፎከሪያቸው ሆኖ ይገኛል። ይህ የታሪክ ስርቆት በአንድ በኩል ደግሞ ሰፊው የትግራይ ሕዝብ ታሪክ እንደሌለው ሕዝብ እንዲያስቆጥረው የተደረገ የመንግሥት መመሪያ ነው። ቢሆንም የትግራይ ህዝብ ቂሙንና ተቃውሞውን በቁጣና
በጥላቻ በብዙ መንገድ ደጋግሞ ገልጾዋል። ይህና ይህንን የመሳሰሉ አድሃሪ ድርጊቶች አሁንም ያለው ፋሽስታዊ መንግሥትም ስለቀጠለበት ሰብዓዊ ክብሩና መብቱ እስኪመለስለት ድረስ ሰፊው የትግራ ህዝብ ትግሉን አያቋርጥም። ጨቋኝዋ የአማራ ብሔርም ጭቆናዋ እስካላቆመች ድረስ ህብረተሰባዊ እረፍት አታገኝም።

II. መፈትሔው

ሀ. ብሔራዊ ትግል

ከብዙ ጊዜ ጀምሮ የትግራይ ብሔራዊ ጭቆና እና በደል አስቆጥቶ ጭቆናውንና በደሉን ከሥሩ ለመንቀል የፖለቲካና የትጥቅ ትግል ሲያካሂድ ቆይቷል። በተለይም ከዘመን ምኒልክ ዘመነመንግሥት ጀምሮ ፀረ-ሸዋዊ የመሳፍንቶች ሥርዓትና ፀረ-ብሔራዊ ተፅዕኖ የሆነ የተደጋገመ ህዝባዊ እንቅስቃሴ አካሂዷል። ለምሳሌም በወያኔ ጊዜ ፀረ-የአማራ ብሔራዊ ተጽእኖ የተደረገው ዲሞክራሲያዊ የትጥቅ ትግል ምን ጊዜም የማይረሳ ነው።

ስለዚህ፦

፩. አሁን ያለው አድሃሪ መንግሥት የብሔሮች ጥያቄ በሚመለከት ጉዳይ ላይ ያለው አድሃሪ አቋም የነበረውን የብሔሮች ቅራኔ እንዲባባስና እንዲከር ስላደረገው፦

፪. እየተባብሰና እየከረረ የሄደው የብሔሮች ቅራኔ ጨቋኝና ተጨቋኝ ብሔሮች በአንድ ዓላማ እንዳይታገሉና መደባዊ ሥምሪታቸውን እንዳያሰፋፉ ትልቅ እንቅፋት ስለሆነ፦

፫. ምንም እንኳን አብዮት ለማካሄድ መላ የኢትዮጵያ ጭቁን ህዝብ ተሳታፊ የሚሆንበት የፖለቲካ ማህበር አስፈላጊ ቢሆንም “ተራማጅ” ነን ባዮች የሸዋ ምሁራን ትምክህተኞችና አድርባዮች ሆነው ስለሚገኙ በአንድ የፖለቲካ ማህበር ሥራ ተረማጅ ዓላማ ይዞ አብዮት ለማካሄድ የማይቻል ስለሆነ፦

ብሔራዊ ጭቆናን ፋሽስታዊ አገዛዝንና ኢምፐርያሊዝምን ለመታገል ጭቁን ብሔሮች መደባዊ ይዞታውን ያልለቀቀ አብዮት (ብሄራዊ የትጥቅ ትግል) ማካሄድ አስፈላጊና ግዴታቸው ሆኖ ያገኙታል። ስለዚህ ነው ጭቁኑ የትግራይ ህዝብም አብዮታዊ ብሔራዊ የትጥቅ ትግል በማካሄድ ላይ ያለው።

ሀ. ዓላማውና ሥራው፡-

የትግራይ ህዝብ ብሔራዊ ትግል ፀረ-የአማራ ብሔራዊ ጭቆና፣ ፀረ-ኢምፐርያሊዝም እንዲሁም ፀረ-ንኡስ ከበርቴያዊ ጠጋኝ ለውጥ ነው። ስለዚህ የአብዮታዊው ትግል ዓላማ ከባላባታዊ ሥርዓትና ከኢምፐርያሊዝም ነፃ የሆነ የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ሪፖብሊክ ማቋቋም ይሆናል።

ለ. የአብዮቱ ጠባዮች፦

በመሠረቱ የአብዮቱ ጣባዮች ፀረ-ባላባታዊ ሥራዓት፣ ፀረ-ንኡስ ከበርቴያዊ ጠጋኝ ለውጥ፣ ፀረ-ብሔራዊ ተጽእኖና ፀረ-ኢምፐርያሊዝም ከመሆኑም በላይ የራስን ዕድል ራስ የመወሰን መብት በመደገፍ ለዲሞክራሲና ለነፃነት የሚታገል አብዮት ነው። ባጭሩ ብሔራዊ ዲሞክራሲያዊ አብዮት (ኤን.ዲ.አር) ነው። የአብዮቱ መሠረታዊ ኃይሎችም ከድሀ ገበሬዎች፣ ከላብ-አደሮችና ከተቆርቋሪ ንኡስ-ከበረቴዎች እንዲሁም ከሌሎች ብሔራዊ ስሜት ካላቸው ክፍሎች ይመነጫል።

ትግሉ ብሔራዊ ዲሞክራሲያዊ አብዮት በመሆኑ የአዲሱ ዲሞክራሲ ፕሮግራሞችን አንደ ፕሮግራሙ አድርጎ ተቀብሏቸዋል። ይህን በመመርኮዝ ተ.ሓ.ህ.ት ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ሕብረተሰባዊና ባህላዊ ዓላማዎቹን እንደሚከተለው ይገለጻል።

በፖለቲካ፦ ፀረ-ባላባታዊ ሥርዓትና ፀረ-ኢምፐርያሊዝም የሆኑት መደቦች በሙሉ የዲሞክራሲያዊ ሪፖብሊክ መንግሥት ያቆማሉ። መሠራታዊ የዲሞክራሲ መብቶች ለጭቁኑ መደቦች ያምንም ገደብ ይሰጣሉ።

ህዝቡ በመንግሥት ስልጣን ተሳታፊ እንዲሆን ተወካዮችን በዲሞክራሲያዊ መንገድ ይመርጣል። ሥልጣኑም የጭቁን መደቦች ይሆናል። ሕዝባዊው መንግሥት የሕዝቡ ደህንነት የመጠበቅና የመደብ ጠላቶቹን የመርገጥ ኃላፊነት ይኖረዋል። ይህም ማለት የዲሞክራሲያዊ መንግሥት ቁሞ በዲሞክራሲያዊ ማእከልነት (ዲሞክራቲ-ሴንትራሊዝም) የተመሠረተ የአስተዳደር ዘይቤ በመከተል የሕዝቡ ሙሉ ተወካይነት እምኖ የፆታ፣ የሃይማኖት፣ የስር-ብሄሮች ወ.ዘ.ተ. ልዩነት እንዳይኖር ማድረግ ማለት ነው።

በኢኮኖም፦ መስፍናዊ ስልተ-ምርት ደምስሶና የኢምፐርያሊዝም ብዝበዛ ከሥሩ ነቅሎ ነፃ ብሄራዊ ኢኮኖሚ ማቆም የመሬት ይዞታውን ሥርዓት ማስተካከልና ከበርቴያዊ ምርት ተቆጣጥሮ የምርት ኃይሎችን በህበረትሰቡ ቁጥጥር ሥር በማድረግ ለህብረተሰብዓዊነት ኢኮኖሚ መንገድ መጥረግና የህዝቡን ጥቅም ለማሟላት ማንኛውም ዓይነት ብዝባዛ የሌለበት የኢኮኖሚ ሥርዓት መመሥረት የተ.ሓ.ህ.ት. የማይታጠፍ ዓላማዎች ናቸው። ጊዜው ያለፈበት የኢኮኖሚ ሥርዓት ባስከተለው ብዝበዛ ምክንያት በሕብረተሰቡ ውስጥ ያሉት መሠረታዊ ችግሮች ድንቁርና፣ ድህነትና ረኃብ የመሳሰሉ እንደዚሁም መደቦችና የመደብ ብዝበዛ ለማጥፋት ተ.ሓ.ህ.ት. የማያቋርጥ ትግል ታደረጋለች።

በባህል፦ አሁን ያለውን አሮጌና አድሃሪ ባህል ደምስሶ በአዲሱ አብዮታዊ ባህል መተካት የተ.ሓ.ህ.ት. ዓላማ ነው። ይህ ባህል ፀረ-ባላባትና ፀረ-ኢምፐርያሊስት ባህል ከመሆኑም በላይ በመደብ ይዞታው የፆታና የንኡስ-ብሔሮች ልዩነት የሌለበት በላብ-አደር ዓለም አቀፍዊነት ላይ የተመሠረተ የዕድገትና የእኩልነት ባህል ይሆናል።

ለ. የትጥቅ ትግል፦

ከላይ የተገለጹት ዓላማዎችን በሥራ ለመተርጐም ትግል በማርክሳዊ-ሌኒናው-ማኦ-ሴቱንጋዊ ርእዮተ-ዓለም የሚመራ ዘመናዊ የደፈጣ ውጊያ ታክቲክና ስትራተጂ የተከተለ እንዲዚሁም ብሔራዊ መንግሥት ለማቆም የሚተልም በጭቁን የትግራይ ሕዝብ የተደገፈ የትጥቅ ትግል ሆኖ እናገኘዋለን።

III. አሳሳቢ በሆኑት ውስጣዊና ዓለም-ዓቀፋዊ ሁኔታዎች ላይ ያለን አቋም።

1. የገጠር መሬት ጉዳይ፦

የገጠር መሬት ጉዳይ በመላው ኢትዮጵያ አሳሳቢ የሆነ የኢኮኖሚ ችግር በመሆኑ በተሎ መፍትሔ ማግኘት አለበት። ችግሩ የጭቁን ህዝቦች ችግር በመሆኑ ለብዙ ጊዜ ተራማጆችን ሲያሳስብ የኖረ አሁንም አብዮታዊ መፍትሔ የሚጠብቅ ጥያቄ ነው። ባላባታዊው የመሬት ይዞታ ስርዓት ለጥቂቶች መሳፍንቶች ምቾት ሲሰጣቸው ለሰፊው ህዝብ ግን መሰደድን ድህነትንና ረኃብን አስከትሏል። እንዲሁም ጭሰኛው ከእርሻ የሚያገኘው ገቢ እያነሰ በሄደ ቁጥር በዚህ አንፃር ደግሞ የሚከፍለው ግብር ከመጨመሩም በላይ በየጊዜው እየናረ የሚሄደው የዕቃዎች ዋጋ ኑሮው እየቆረቆዘ አንዲሄድ አድርጎታል። “መሬት ላራሹ” የሚለው ዲሞክራሲያዊ የህዝብ መፎከር የመሬት ይዞታና ችግር መፍትሔ እንዲያገኙ የሚጠይቅ ነው። መፈክሩ ተደጋግሞ በህዝቡ ይጠቀስ እንጅ ችግሩ እስካሁን ድረስ መሠረታዊ መፍትሔ አላገኘም።

ባላባታዊ ሆኑ በዝምድና ላይ የተመሠረተው ርስት የሚባለው የመሬት ይዞታ ያስከተለው ችግር በትግራይ አሁን ያለው ሁኔታ በመመልከት መረዳት እንችላለን። መሬቱ በጊዜ ብዛት እየተቆራረጠ ለአንድ ሰው ወይም ቤተሰብ በተለያዩ ቦታዎች ይሰጠዋል። የዚህ ዓይነት የመሬት ሥሪት ኑኖው በእርሻ ላይ በተመሠረተ ህዝብ ላይ ግልጽ የሆነ የእርሻ ችግር አስከትሏል።

እላይ በተገለጸው ምክንያትና ተፈጥሮ ባስከተላቸው ችግሮች ከእርሻ የሚገኘው ገቢ እያደረ ሲቆረቁዝ የህዝቡ ብዛትና የሚከፍለው ግብር (ታክስ) ግን እያደረ ስለሚጨምር ሕዝቡ በየጊዜው በረሃብ ይሰቃያል። በተጨማሪም በመሬት ክርክር ምክንያት በየፍርድ ቤቱ ይንከራተታል። ብዙ ሰውም አገሩን ለቆ ወደየከተማው ይሰደዳል። ከተማ ገብቶ ሥራ ስለማያገኝ ሴቶች ወደ ሽርሙጥና (ሴት አዳሪነት) ሲያመሩ ወንዶቹ ደግሞ ወደ ሌብነትና ማጅራት መችነት ያመራሉ። የቀረቱ ቁጥራቸው ከ-እስከ ሊባል የማይቻል ሰዋች በረኃብና በበሽታ ያልቃሉ። ስለዚህ ይህንን ከባድ ችግር በምን ዓይነት መፍትሄ ሊገኝለት ይገባል? የሚል ጥያቄ ያጋጥመናል። ችግሩ በአብዮታዊ መንገድ መፍትሄ ሊያገኝለት የሚሞክር ፕሮግራም ሁሉ የግድ የሚከተሉትን ሥራዎች ማከናወን ይገባዋል።

1ኛ. የጉለተኝነት የኢኮኖሚያዊ መሠረት ማጥፋትና ባላባታዊ መደብ በመደብነቱ እንዳይኖር ማድረግ፦

2ኛ. ለህብረተሰባዊ ዕድገት መንገድ መጥረግ። እነዚህን ሥራዎች ማከናወን ማለት ደግሞ ጨሰኛና ጉልተኝነት ማጥፋት፣ የመሬት ይዞታን ማስተካከል፣ የህብረት እርሻ ማስፋፋት፣ ጭቁኑን ወዝ-አደር ማደረጀትና ፖለቲካዊ ትምህርት መስጠት ማለት ሆኖ እናገኘዋለን። በተጨማሪም የመሬት ክርክር ማጥፋት። በየባላገሩ የሚገኘው የሥራ ማጣት ችግር ማቃለል። በእርሻ ላይ የተመሰረቱ ትንንሽ እንዲስትሪዎች ማቋቋም እስፈላጊ ናቸው። ከላይ ከተጠቀሱት ነገሮች እሥራ ላይ ለማዋል የሚቀጥሉት ነገሮች በቅድሚያ መሟላት አለባቸው።

1ኛ. አስፈላጊው የፖለቲካ መብትና መመሪያ ለሰፊው ህዝብ የሚሰጥ፣ የሰፊው ህዝብ ጥቅም በእውነት የሚጠብቅ በላብ-አደሩ የሚመራ ጊዜያዊ አብዮታዊ መንግሥት ማቋቋም።

2ኛ. ፕሮግራሙ እሥራ ላይ ለማዋል ያሚያስፈልጉ የሰው፣ የገንዘብና ወይም ሌላ የማንኛውም ማቴርያል ዝግጅት ማጠናቀቅ።

በዚህ አንፃር አድሃሪው የንኡስ-ከበርቴ መንግስት ይህንን ችግር እንዴት ለማቃለል እንደሞከረ እንመርምር። መንግስቱ በዚህ ረገድ ባወጃቸው አዋጆች አንጻር ስንመለከተው የምሬት ይዞታ ችግርና ባሕረ-ሃሳባዊ መፍትሔው የገባው ይመስላል። ጠለቅ ብለን ስንመረምረው ግን መፍትሄው በወረቀት ብቻ ተወስኖ እንዲቀር የታለመ መሆኑን እንገነዘባለን። ዋናው ቁምነገር ደግሞ ብሔራዊ መፍትሔው ማውቅ ብቻ ሳይሆን ችግሩን ለመፍታት አብዮታዊ ፍላጎትና ስሜት መኖሩ ነው። ይህ ማለትም አስፈላጊ የሆኑት ፖለቲካዊ፣ ድርጅታዊ የገንዘብና የሰው ጉልበት ሌሎችም አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን ማሟላት ነው።

አዋጁ ስለ ……

1. ርስት

ሀ. “በዚህ ሥርዓት ውስጥ የሚገኘው መሬት የማይሸጥና የማይለወጥ ስለሆነ ለህዝቡ የመኖር ዋስትናና ክብርን ሰጥቶ እንደቆየና አብዛኛው ህዝብ ከሞላ ጐደል በእኩልነት እንደሚተዳደር ግልጽ ነው።”

ለ. “የኢትዮጵያን ህዝብ ሕብረትና ወንድማማችነት በበለጠ ለማጠናከር በኢትዮጵያ የሚገኘው የመሬት ይዞታ አንድ ማድረግ ያስፈልጋል። በአስተዳደርም በኩል ቢሆን በአንድ አገር ህዝብ ተመሳሳይ ሕግ ማውጣት ጠቃሚ ነው።” ይላል።

ይህ ጉልታዊ ሥርዓት ለህዝቡ የመኖር ዋስትና ሰጥቶታል ብሎ ማወጁ ሥርዓቱ የፈጠረውን ግልጽ ድህነትና ረሃብ መካድ ማለት ነው። ግልጽ የሆነ የመደብ ቅራኔና ልዩነት እያለ አብዛኛው ህዝብ በእኩልነት እንደሚተዳደር ግልጽ ነው ብሎ ማለት ችግሩን ለማጥፋት ብቻ ሳይሆን መሠረት ለሌለው ህብረትና ወንድማማችነት ተብሎ ለተለያየ የመሬት ይዞታ ችግር አንድ አይነት አዋጅ ማወጅ መንግሥቱ ለማወናበድና ለማጨበርበር የሚያደርገውን ሙከራ ግልጽ አድርጎ ያሳያል። ለችግሩም አብዮታዊ መፍትሄ ለማምጣት ስሜትና ፍላጎት እንደለሌው ያስረዳል።

2. የገበሬዎች ማሕበሮች በአዋጁ መሠረት ሥራና ዓላማቸው እንደሚከተለው ተዘርዝሮ እናገኘዋለን።

ዓላማ፦

ሀ. “በህብረተሰባዊ ፍልስፍና መሠረት የጪሰኞችና የድሀ ገበሬዎች ፖለቲካዊ መብትና ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለመጠበቅና ለማስፋፋት”

ለ. “ህብረተሰብዓዊነትን ሥራ ላይ ለማዋል በሚደረጉት እርምጃዎች ተካፋይ እንዲሆኑ ከህብረተሰቡ ተረማጅ ክፍሎች በተለይም ከላብ-አደሩ ማህበሮች ጋር መተባበርና መተሳሰር።”
ሥራ፦

ሀ. “መሬት የግል ይዞታ በሆነባቸው ቦታዎች ሁሉ መሬቱን በትክክልና ያላንዳች አድልዎ ለጭሰኞችና ለድሀ ገበሬዎች ማደል።”

ለ. “በርስትና በዘላን መሬቶች ላይ አስፈላጊ የሆኑት የህብረት ሥራዎችና ድርጅቶች ማካሄድ።

ሐ. ማደራጀት፣ ምርጫ ማካሄድ፣ ፖለቲካ ትምህርት መስጠት፣ የፖልቲካና የአስተዳድር ሥራዎች ማካሄድ የአካባቢው ሕብረተሰባዊ ሕጋዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ማቃለል።”

ይሁን እንጅ ከላይ የተጠቀሱትን አብይ ጉዳዮች ለማካሄድ የተወሰኑ ድርጅቶች የተቋቋሙት በደንብ ባልተደራጀ መንግድ የፖለቲካ ንቃታቸው በጣም ዝቅተኛ በሆነ የሥራ ልምድ በሌላቸው ወታደሮችና በዘመቻው በማያምኑ ተማሪዎች እንዲሁም በአካባቢው ጭቃ ሹሞች ነው።

መመሪያቸው የሚያገኙት ከዚህ ይባስ ብሎ ደግሞ ይህ የማደራጀትና ፖለቲካዊ ትምህርት የማካሄድ ሥራ የሚከናወነው ጥቂት የአድሃሪው መንግሥት አባሎች “ደርግ” ባወጡት መመሪያ መሠረት ነው። እነዚህ ጥቂት አወናባጆች ህብረተሰብዓዊነትን የሚያውቁት በቃል እንጂ በግብር ካለመሆኑም በላይ ይህ የሚያሳፍር እውቀታቸውም ቢሆን ለማወናበድ እንጂ ቁምነገር ለመሥራት አይጠቀሙበትም። በተጨማሪ ደግሞ አድሃሪው ደርግ የኢትዮጵያ ላብ-አደሮች ኮንፈደረሽን አውድሞ በምትኩ አድሃሪ የሆነ የላብ-አደሮች ማህበር አንዲመሠረት በማድረጉ የተባለው የሠራተኛ ማህበር መሠረት ነስቶት ይገኛል። ይህ የሚያሳየኝ እነዚህ የገበሬ ማህበሮች በወረቀት ላይ የሠፈረውን ዓላማና ሥራ በግብር ለመተርጎም ሳይሆን የተባለው ዓላማና ሥራ በወረቀት ላይ ብቻ ተወስኖ እንዲቀርና የመንግስቱ ወኪሎች የሆኑ የመንግሥቱ ሥራዎችና ፍላጎት ለማሟላት መመስረታቸው ነው። ስለዚህ የጭሰኞችና የድሃ ገበሬዎች የፖለቲካና የኢኮኖሚ ፍላጎት ለማሟላት አልተመሰረቱም ማለት ነው።

3. ታላላቅ እርሻዎች

1. አዋጁ ስለነዚህ እርሻዎች

ሀ. የመንግሥት እርሻዎችና የህብረት እርሻዎች እስኪደራጁ ድረስ መንግሥቱ እነዚህን ታላላቅ እርሻዎች በመሰለው መንገድ ያስተዳድራል። በተጨማሪም መንግሥት በመሰለው መንገድ እስኪያስተዳድራቸው ድረስ የነዚህ ታታላቅ እርሻዎች ባለቤቶች ማስተዳደራቸውን ይቀጥላሉ።

ለ. በየመሥሪያ ቤቱ እንዲሰራጭ በተሰጠው መግለጫ መሠረት ደግሞ እነዚህን ታላላቅ እርሻዎች ለመካፈል የሚፈልጉ ገበሬዎች የሉም በሚል ምክንያት እነዚህ እርሻዎች ለባለቤቶቹ ወይም ለሌላው ሰው በኪራይ ሊሰጥ እንደሚችል እንገነዘባለን። በተጨማሪም የተወረሱት ታላላቅ እርሻዎች ያስተዳደርና የቴክኒክ ጉድለት ይፈጥራል በሚል ምክንያት በማህበር መካሄዳቸው ቀርቶ በመንግሥት ሥር እንዲተዳደሩ ተደርጓል።

መንግስቱ ታላላቅ እርሻዎችን በመሰለው መንገድ ያስተዳድራል የሚለው ሃሳብ በደርጉ አንፃር ስንመለከተው ደርጉ እነኝህን አርሻዎች ለኢምፐርያሊስቶች በኮንሰስዮን ሊሸጠላቸው እንደሚችል አንረዳለን። ስለዚህ አድሃሪው መንግሥት አዋጁን በሥራ ላይ ለማዋል የሚያስፈልጉትን ነገሮች ስላላሟላና ለማሟላትም ስለማይችል የመንግሥቱ መውደቅና በተራማጅ መንግሥት መተካት አስፋላጊ ሆኖ እናገኘዋለ።

2. የከተማ ቦታና የትርፍ ቤቶች ጥያቄ

ያላንዳች ጥርጥር በመላው ኢትዮጵያ የሚገኙት የከተማ ቦታዎችና ቤቶች በጥቂት መኳንንት፣ ከበርቴዎችና ቡችሎቻቸው እጅ ለብዙ ጊዜ ቆይተዋል። ስለዚህ የቤት ክራይ፣ የከተማ ቦታ ዋጋና የቤት ማሠርያ ዋጋ በየጊዜው ከመጠን በላይ እየናረ ስለሄደ በከተማው ሕዝብ ላይ ታልቅ ውድቀትን አስከትሏል። እንዲሁም እነዚህ የገዥው መደብ አባሎች መጠን የሌለው የግል ንብረትና ከዚሁ የሚመነጩ መብቶች አግኝቷል። ከግብር ነፃ ከመሆናቸውም በላይ ባስፈለጋቸው ጊዜ ያስፈለጋቸውን ኃይል በመጠቀም የፖለቲካ ሥልጣን አግኝተው ሕዝቡን ለመርገጥና ለመበዝበዝ ተጠቅመውበታል። በዚህ ምክንያት አብዛኛው የከተማ ህዝብ የከተማ ቤትና መሬት የማግኘት መብቱ ተነፍጎ በቤት ኪራይ ተሰቃይቷል። በዚህ ጊዜ ነው ለእንደዚህ ዓየነት ችግር አስፈላጊ፣ ትክክለኛና የማያዳግም መፍትሔ ሊፈለግለት የሚገባው፡፡ ይሁን እንጅ አድሃሪው መንግሥት ችግሩን በሕዝቡ ፍላጎት መሠረት በማጥፋት ፋንታ ከጥቂት ገዥዎች ፍላጎትና ያለሙሉ አብዮታዊ ስሜት ለፕሮፖጋንዳው ጥቅም ብቻ አዋጅ
በማወጅ ችግሩ አንዳለ ቀጥሏል።

ይህንን ለማለት የቻልነውም፦

1ኛ. መንግሥቱ ባወጀው አዋጅ ምክንያት የቤቶች ሥራ እንዱስትሪ መበላሸተና ይህም የአገሪቱን የኢኮኖሚ ዕድገት ወደኃላ የሚጎትት ሆኖ በመገኘቱና የቤቶች ሥራ እንዱስትሪ በመንግሥት ወይም በሕዝቡ ማህበሮች የሚካሄድበትን መንገድ ተዘጋጅቶ ባለመቆየቱ ነው። ይህም ሊሆን የቻለው የከተማ ቦታና ቤት በጥቂት ሰዎች እጅ በመኖሩ ይህንን ታላቅ ሥራ ለማካሄድ የመንግሥቱ ተካፋይነት አስፈላጊ ስለሆነ ነው። ሆኖም መንግሥቱ በዚህ ረገድ ፈጽሞ አልተዘጋጀም።

2ኛ. ይህ የቤቶች ሥራ መቋረጥ በቀጥታ ለሚመለከታቸው ሠረተኞች (ግምበኞች) ብቻ ሳይሆን በተዘዋዋሪ መንገድም ለቤት ሥራ የሚያገለግሉ ዕቃዎች በሚሠሩ ፋብሪካዎችና ድርጅቶች ውስጥ ያሉትንም ሠራተኞች የሥራ ማጣት ችግር አስከትሎባቸዋል። ከዚህ አልፎም በ1-2 ክፍል ቤት ውስጥ ይኖር የነበረው ቤተሰብ ከመንግሥቱ ጋር ባነሳው እልህ ምክንያት 7-8 ክፍሎችን ስለያዘ በየከተማው በብዙ ሽህ የሚቆጥር ህዝብ ኑሮውን በሆቴል ውስጥ መስርቶ ከድሮው በባሰና ቅጥ በሌለው ምዝመዛ ሲሰቃይ ይገኛል።

3ኛ. ከጊዜ ወደ ጊዜ እየናረ የሚሄደው የዕቃዎች ዋጋ እንፃር ስንመለከተው የቤት ኪራይ ለመቀነስ የተወሰደው እርምጃ የማያዳግም መፍትሔ ሳይሆን ጊዚያዊ እርጥባን ሆኖ እናገኘዋለን። ይህ የሚያስረዳን እንደዚህ ዓይነት የተደራረበና ከባድ ችግር ሊወገድ የሚችለው በአፍ አዋጅ ሳይሆን ከሰፊው ህዝብ የመነጨ የሰፊው ህዝብ መንግሥት ሲመሠረት ብቻ ነው።

3. የኤርትራ ጥያቄ

የኤርትራ ጥያቄ መንስኤው ምንድነው? ለዚህ ጥያቄ መሠረታዊ መልስ ለመስጠት የሚከተሉትን ታሪካዊ መረጃዎች መመልከት ያስፈልጋል።

ሀ. ሁለት ህዝቦች፣ ሀገሮች ወይም ብሄሮች በተለያየ ጊዜ የየራሳቸውን አስተዳደር ይዘው ቆይተው አንዱ ባንዱ ላይ የሚያደርገው በሃይል የተደገፈ ግዛት የቅኝ እገዛዝ ተግባር ነው።

ለ. እንዲሁም ሁለት ሀገሮች በሁለቱም ፈቃድና ፍላጎት የየግላቸው መብት ጠብቅው ከተባበሩ በኋላ እንደኛው ሌላውን ቢያምጽ እርምጃው የቅኝ አገዛዝ እርምጃ ነው።

እላይ በተጠቀሰው ታሪካዊ ሃቅ መሠረት የኤርትራ ጉዳይ ስንመረምር የሚከተሉት ነገሮች ያጋጥሙናል።

ሀ. በ1890 ዓ.ም አካባቢ ኤርትራና ኢትዮጱያ ለየብቻቸው የተለያየ አስተዳደር ይዘው ይኖሩ ነበር። ይኽውም ኤርትራ እንደ የኢጣሊያ ቅኝ ግዛት ኢትዮጵያ ደግሞ እንደ አንድ “ነፃ” አገር ሆነው የኖሩ ነበር።

ለ. በ1952 ዓ.ም ኤርትራ ከኢትዮጵያ ጋር በፌደረሽን መተዳደር በጀመረችበት ጊዜ ሁለቱም ሀገሮች ያደረጉት ስምምነትና የተባበሩት መንግሥት ውሳኔ ኤርትራ ራሷን የቻለች አገር መሆንዋን ይጠቅሳል።

ሐ. ይሁን እንጅ በ1962 ዓ.ም ኢትዮጵያ በኤርትራ ላይ የወሰደችው እርምጃ ስምምነቱ “አንደኛው ወገን ብቻ ለተባበሩት መንግሥታት ሳይጠየቅ ሊጥሰው አይችልም።” የሚለውን ሕግ በግለጽ የሚፃረር ሆኖ ይገኛል።

ስለዚህ ኤርትራ ውስጥ የሚደረገው ትግል ያላንዳች ጥርጥር ሃቀኛና ታሪካዊ መሠረት ያለው ፀረ- ቅኝ አገዛዝ ትግል ነው።

4. የኢትዮጵያ አብዮት

ሀ. በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙትን ሁኔታዎች ስንመረምር ህዝባዊ አብዮት ከፀረ-አብዮታዊ ደርግ ጋር ብርቱ የትንንቅ ትግል በማድረግ ላይ መሆኑን እንገነዘባለን። ንኡስ-ከበርቴያዊ ፋሽስታዊ ደርግ መላው የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሥልጣን ጨብጦ እውነተኛ ተራማጆችን በግፍ በመግደል ላይ ይገኛል። ህዝቡን ለመደለልና አብዮታዊ ለመምሰል ተንኮል ያዘሉ ባዶ አዋጆችን እያወጀ ፀረ-አብዮታዊነቱን ለመሸፈን ሞክሯል። ሆኖም ይህ ተንኮል ውሎ አድሮ በመገለጹ ህዝቡ ከአብዮታዊ ግስጋሴው ፍንክች አላለም። ምክንያቱም የደርጉ ባዶ አዋጆች የሰፊውን ህዝብ አብዮት ጥያቄዎች ስላልመለሱና ሊመልሱም የማይችሉ ስለሆነ ነው። የሰፊው ህዝብ ፍላጐት ሊሟላ የሚችለው በብሔራዊ ዲሞክራሲያዊ ብቻ ነው።

ለ. ከዚህ የተመሰቃቀለ ኑሮ መውጫ በር ግልጽ ነው። ይኽውም የብሔሮች የትጥቅ ትግል ወይም በመላው ኢትዮጵያ የሚካሄድ የፖለቲካ ትግል ማከናወን ናቸው። የትኛውን መንገድ መከተል እንደሚገባ የሚያዘው ግን በየቦታው የሚገኘው ተጨባጭ ሁኔታ ነው። ሁለቱም መንገዶች የብሔራዊ ዲሞክርሲያዊ አብዮት አመራር ተከትለው ሳይንሳዊ ህብረተሰብዓዊነትን ለመገንባት ማቀድ አለባቸው። እነኚህ ሁለት የትግል መንገዶች ተባብረው ሥራቸውን እንዳያካሂዱ አብዮታዊያን ነን ባዮች የአማራ ብሔር ትምክህተኝነትና ጠባብ ብሄርተኝቶ ያጠቃቸው ሰዎች አግደውት ይገኛሉ። “ህብረተሰብዓዊነት ሲባል” ከደርጉ መተባበር ያስፈልጋል በማለት “ቀድሞ የነበረውን የመንግሥት ስርዓት ሙሉ በሙሉ ባይወድም አዲስ ህብረተስብዓዊ ሥርዓት መመሥረት አይቻልም።” የሚለውን ታሪካዊ ማርክሳዊ ሃቅ ይክዳሉ። የተለያዩ ብሔሮች አብረው ባሁኑ ጊዜ ለብሔራዊ ዲሞክራሲያዊ አብዮት ሊታገሉ ይችላሉ በማለት በጊዜው ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ያልተደገፋና የአማራን ብሔር ጭቆና በሽፍንፍን ለማቆየት የታለም የትምክህተኞች ተንኮል ደግሞ በሌላ በኩል ይነዛሉ። እነኚህ የአፍ ሊቃውንት አወናባጅነታቸው እንዳይነቃባቸው በታሪክ የተደገፉትን የብሔሮች ትግል በስመ ጠባብ-ብሔርተኝነት ሲያኳስሱ ይታያሉ። እንደዚህ ዓይነቱ አጉል መራቀቅና ትምክህተኝነት በኢትዮጵያ ውስጥ ያለው አብዮታዊ እንቅስቃሴ ሊያደበዝዙትና ሊያደናቅፉት በቅቷል። በአሁኑ ጊዜ ሰፊው ህዝብ ተደራጅቶ አብዮት ለማካሄድ ጊዜው ፈቅዶለት እያለ ማወናበድና አጉል መራቀቅ በህዝብ ላይ የተፈጸመ ታላቅ ታሪካዊ ክህደት ነው።

5. ኢምፐርያሊዝምና ሦስተኛው ዓለም

በዓለም አቀፍ አድሃሪነቱ ለአብዮታዊ ግስጋሴዎች አንቅፋት የሆነው ኢምፐርያሊዝም የሦስተኛው ዓለም ሕዝቦችን በእጅ አዙር በመግዛትና በመጨቆን ላይ ያለው በየአገሩ ካሉት ቡችሎች በመሻረክ ነው። ኢኮኖያዊ ምዝበራ የሚያካሂደው እርዳታ እተባለ ከኢምፐርያሊስት አገሮችና ከአንዳንድ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች (የዓለም ባንክ) የዓለም የገንዘብ ድርጅት (አይ.ኤም.ኤፍ) በሚሰጠው የተሸፈነ መርዙ አቋሙ በተዛባ የንግድ ልውውጥና ጥሬ ሀብቶችን ያለአግባብ በመዝረፍ ነው።

ፖለቲካዊ ጭቆናም የሚያካሂደው በዓለም ዙሪያ ባቋቋማቸው ወታደራዊ ሠፈሮቹና በውጭ ጉዳይ አመራሩ ነው። የሦስተኛው ዓለም ህዝቦች በኢምፐርያሊዝምና በየአገሩ በሚገኙ ቡችሎቹ ላይ ገሀድ ጦርነት ካወጀ ቆይተዋል። የነዚህ ሕዝቦች ትግል በየቀኑና በየሰዓቱ ወደ ድል በመቃረብ ላይ ነው። ካምቦዲያ፣ ጊኒ-ቢሳዋ፣ ሞዛምቢክ፣ ቬትናም ወ.ዘ.ተ. በኢምፐርያሊዝም ላይ ያገኙት ድል ኢምፐርያሊስቶችን አዳክሟቸዋል። ይህ የኢምፐርያሊዝም ውድቀት ዓለም አቀፍ አብዮትና የህብረተሰባዊነት ድል ማለት ነው። የኛ ትግልም ከነዚህ ህዝቦች ትግል ሊነጠል የማይችል ተራማጅ ትግል በመሆኑ ከነዚህ ጭቁን ህዝቦች ትግል ብዙ እነማራለን። የግራ እጆቻችንም በማንሳት ህብረታችንን እንገልጽላቸዋለን።

6. የውጭ ጉዳይ አመራር

እላይ እንደተገለጸው ሁሉ እንቅስቃሲያችን የዓለም ህብረተሰባዊ ዲሞክራሲያዊ እንቅስቃሴዎች አካል ነው። ስለሆነም ለዓለም አቀፍ ኢምፕርያሊዝም ያለው ጠንካራ ተቃውሞና ለተራማጅ እንቅስቃሴዎች ያለው ድጋፍና ተባባሪነት ይገልጻል። በውጭ ጉዳይ አመራሩ የወዝ-አደር ዓለም አቀፍነት ይከተላል። ጠባብ ብሄርኝነተና ትምክህተኝነት በጥብቅ ይቃወማል።

ስለዚህ ተ.ሓ.ህ.ት

1. ካላንዳች የፖለቲካ ተጽዕኖ ከግለሰቦች፣ ወይም ከማህበሮች እንደዚሁም አገሮች የሚሰጠውን ማንኛውም የሞራልና የማቴሪያል ድጋፍ በደስታ ይቀበላል።

2.ቅኝ አገዛዝ የእጅ አዙር ቅኝ አገዛዝና ኢምፐርያሊዝምን በመቃወም ላይ የሚገኙትን አፍሪካውያን ወንድሞቹን መደገፍ ብቻ ሳይሆን ከነሱ ጋር እጅ ለእጅ ተያይዞ ትግሉን ያካሂዳል።

3.ፅዮናዊያንና ኢምፐርያሊስቶችን በተለይም የአሜሪካ ኢምፐርያሊስቶችን በመቃወም ላይ ከሚገኙ ፍልስጤማዊያንና የዐረብ ህዝቦች ጋር ግንኙነቱን ያጠናክራል።

4.የሮደሽያንና የደቡብ አፍሪካን ዘረኛ መንግሥታት በጥብቅ ያወግዛል።

5.ለዲሞክራሲና ለህብረተሰብ ዓዊ ዕድገት በመታገል ላይ ለሚገኙት የላቲን አሜሪካና የኢሲያ ህዝቦች ያልተቆጠበ የሞራል ድጋፍን ይሰጣል።

ፋሽሽታዊ ደርግ ይውደም!

ድምቀት ለዓልም ተርማጅ ሃይሎች!

የትግራይ ትግል ህዝብ ያሸንፋል!!

——- •••••• ——-

ትሕዝቶ ቅኑዕ ብሄራዊ ቃልሲ በደባዊ ቃልሲ ኢዩ፤

Genuine National struggle is in ESSENCE class struggle

ኣብ ጭኩናት ብሄራት ካብ ዝርክብ ህዝቢ ብዝኽፋአ ዝሳ ቕዩ እትም ዝምዝመዙ ርሂፀ-በለዓትን ሓረስቶትን ከምኡ’ውን ካልኦት ብሽቕሊ ዝናበሩን ኢዩም። እዚ ድማ ብሄራዊ ጭኮና መደባዊ ጭኮና ምዃኑ ስለዘርእየና . . . . ኣንፃር ብሄራዊ ጭኮና ዝግበር ቃልሲ’ውን ኣንፃር መደባዊ ጭኮናን ኣንፃር መድሐርሓርትን ጠካማትን ተወለድቲ ናይ’ታ ብሄር ዝግበር ቃልሲ ምዃኑ ዘይጠራጥር ሓቂ ኢዩ።

Among the people of the oppressed nationalities, those who actually suffer are mainly the oppressed
and exploited classes, the workers, peasants and other labouring classes. From this we can see that
national oppression is in reality class oppression, and that the struggle against national oppression
is in reality a struggle against class oppression and often simultaneously a struggle against the
reactionaries and traitors of one’s own nationality.

ብሄራዊ ማዕርነትን ሙሉእ ናፅነትን ንምርካብ ውፅዑ ህዝቢ ትግራይ ብተ.ሓ.ህ.ት. ተሰሪዑ ዘይሕለል ብሄራዊ ዲሞክራሲያዊ ቃልሲ ብምክያድ ነቲ ኣስካሕኪሕዎ ዘሎ ብሄራዊ ጭኮና ሃፀያዊያንን ግዝኣት ኮራኹሮምን ክድምስሶ ኢዩ። ከማኡ’ውን መደብ መዝመዝትን ስርዓት ምዝመዛን ካብሱሩ ንምብርቋቕ እቲ ቃልሱ ናብ ዴሳዊ ቃልሲ አሰጋጊሩ ናይ ሓርነት ኩታ ክጉምሳም’ዩ።

In order to achieve a national equality and total emancipation, the oppressed people of Tigray
nationality, under the guidance of T.P.L.F will resolutely carryout national democratic revolution,
put an end to the national oppression of the imperialists and overthrow the rule of their lackeys,
they will then carry through the socialist revolution and destroy all the exploring classes and system.

T.P.L.F.

Check Also

በአሜሪካን ሀገር የምትኖሩ የአማራ ማህበራትና የአማራ ልጆች የት ነው ያላችሁት?? Share!

ድሮን ሲያስተኩስ የነበረው ባንዳ በፋኖ ተያዘ ! እኔን ያየህ ተቀጣ !

News in Pictures

Time in Ethiopia

Multi threaded Redundant Dedicated Server in USA and in Europe.