Breaking News
Home / Amharic / የጣና ሀይቅ ችግሮችና መፍትሔዎቹ !

የጣና ሀይቅ ችግሮችና መፍትሔዎቹ !

በ Muluken Tesfaw

ከአገራችን ትልቁ የሆነው የጣና ሀይቅ ከ40 በላይ ትንንሽ ጅረቶችና ሰባት ዓመቱን በሙሉ የሚፈሱ ወንዞች ገባር ሆነው ገብተው አንድ ትልቅ ወንዝ እንደገና ከሀይቁ ይነሳል፤ ዓባይ ነው፡፡ ወደ ሀይቁ ከሚገቡት ወንዞች ዋና ዋናዎቹ ግልገል ዓባይ፣ መገጭ፣ አርኖ ጋርኖ፣ ርብና ጉማራ ይገኙበታል፡፡ የዓባይ ወንዝ ከእነዚህ ወንዞች ሁሉ ተጠራቅሞ ከባህር ዳር እስከ አሌክሳንድሪያ ዴልታዎች የ1450 ኪሌ ሜትሮችን በመጓዝ ወደ ሜዲትራኒያን ባህር ይጨመራል።

ጀምስ ብሩስ በ18ኛው ክ/ዘመን የዓባይ ወንዝን መነሻ ለማጥናት ሲመጣ ከ37-45 የሚሆኑ ሰው የሚኖርባቸው ደሴቶች እንደነበሩ ይታመናል፡፡ ከሀይቁ ወደ ዳር በኩል የነበሩ ደሴቶች ሀይቁ እየሸሸ ሲሄድ የእርሻ ቦታዎች ሆነው ቀርተዋል፡፡ የክርስቶስ ሠምራ ገዳምን ማየት ይቻላል፡፡ የጣና ሀይቅ እስከ 1980ዎቹ መጀመሪያ ድረስ የፋሲል ግንብ ሰገነት ላይ ተሁኖ በቀላሉ ይታይ ነበር፡፡ የደቅ ደሴት የጣና ሀይቅ ትልቁ ደሴት ሲሆን ወደ 5k የሚጠጉ ገበሬዎች ይኖሩበታል፡፡

የጣና ሀይቅ የኅልውና ችግሮች በቅደም ተከተል፤

1) የጣና በለስ የኃይል ማመንጫ፤

የጣና በለስ የኃይል ማመንጫ የተገነባው የዓባይ ወንዝ መውጫው ላይ በመገደብ (ጨረጨራ) በበለስ በኩል አዲስ መውጫ (ከተፈጥሯዊው ውጭ) በመቀነስ እንዲፈስ በማድረግ ነው፡፡ የጣና ሀይቅ አሁን በዓባይና በበለስ በኩል በሁለቱም አቅጣጫ ስለሚፈስ የውኃውን መጠን ቀንሶታል፡፡ ከ2002 ዓም የኃይል ማመንጫው ከተጀመረበት ጊዜ በፊት ከነበረው የሀይቁ ጥልቀት ከ50 ሳሜ እስከ 1 የሚሆን አማካይ ጥልቀት እንደቀነሰ ይፋ ያልሆኑ ጥናቶች ያሰያሉ፡፡ የሳትላይት መረጃዎች እንደሚያሳዩት አሁን ያለው የጣና ሀይቅ ስፋት ከ3200 ካሬ ኪሎ ሜትር አይበልጥም፡፡ የጠፋው የሀይቁ ስፋት የስምጥ ሸለቆ ሀይቆች በአንድ ላይ ሆነው የሚኖራቸውን ስፋት የበለጠ ነው፡፡ ከሁሉም ችግሮች በላይ ይህ ፕሮጀክት የሀይቁን ኅልውና አደጋ ላይ ጥሎታል፡፡

2) የእንቦጭ አረም (Water hyacinth invasion)

የእንቦጭ አረም እንዴትና መቼ ወደ ሀይቁ እንደገባ በደንብ አይታወቅም፡፡ ሆኖም አረሙ የደቡብ አሜሪካ ዝርያ እንደሆነ የታመነ ነው፡፡ በቅርብ ያሉ ዳታዎችን ማግኘት ባይቻልም አረሙ ከ24k ሄክታር በላይ የሆነው የሀይቁ አካል በእንቦጭ ተወሮ ነበር፡፡ እምቦጭ በአጪር ጊዜ ብዙ ቦታዎችን የመሸፈን አቅም አለው፡፡ በዚህም በርካታ የሀይቁ አካባቢዎች ደርቀው ገበሬዎች ባህር ሸሹን ቦታ እያረሱት ነው፡፡

3) ከከተሞች የሚገቡ ቆሻሻዎች፤

የባህር ዳር እና የጎንደር ከተማ ቆሻሻዎች ሙሉ በሙሉ በሚባል መልኩ ወደ ጣና ሀይቅ ይገባል፡፡ በባህር ዳር አንዳንድ ሆቴሎች፣ ሆስፒታል፣ መኖሪያ ቤቶች ወዘተ የሽንት ቤታቸውንና የቆሻሻ ማስወገጃ ቱቧቸውን ወደ ሀይቁ ያገናኙ ናቸው፡፡ የጎንደር ከተማ ቆሻሻ ሙሉ በሙሉ በወንዝና በጎርፍ ተጠርጎ ወደ ሀይቁ የሚገባ ነው፡፡ ቆሻሻው ደግሞ ለእንቦጭ አረም መራባት ጥሩ አጋጣሚን ፈጥሯል፡፡
4) በአፈርና በደለል መሞላት

የተፋሰስ ሥራዎች አነስተኛ በመሆናቸው ምክንያት ከደቡብና ማዕከላዊ ጎንደር ተራራማ አካባቢዎች ተጠራርጎ የሚገባው አፈር የሀይቁን ዳርቻዎች በደለል እንዲሞላ አድርጎታል፡፡

መፍትሔዎቹ፤

1) የጣና በለስ የኃይል ማመንጫ ፕሮጀክትን ማቋረጥ፤

አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ርእሰ መስተዳደር በነበሩ ጊዜ በአካል ሳገኛቸው ያነሳሁላቸው ጥያቄ አንደኛው ሀይቁን እየጎዳው ያለውን የጣና በለስ ፕሮጀክት መቋረጥ ቢችል የሚል ነበር፡፡ ይህ ሀይቁን በከፍተኛ ሁኔታ እየጎዳ ያለ የኃይል ማመንጫ ከዚህ የሚመረተውን ኃይል ሊተካ የሚችል አማራጭ ተፈልጎ መቋረጥ መቻል አለበት፡፡ አሊያ ግን በዓመታት ሂደት ሀይቁ ተረት መሆኑ አይቀርም፡፡

2) የእምቦጭ አረምን በመከላከል ስኬታማ ሥራ የሠሩት ኬንያ፣ ኡጋንዳና ታንዛኒያ ናቸው፡፡
የቪክቶሪያ ሀይቅ በእምቦጭ አረም ከጣና በላይ ተወሮ ነበር፡፡ ነገር ግን በማኅበረሰብ አቀፍ ንቅናቄ፣ እምቦጩን ለኢኮኖሚ በመጠቀምና በማስወገድ ሥራ አገሮቹ ስኬታማ ሥራ አከናውነዋል፡፡ እምቦጭን ማጥፋት ከዐሥርት ዓመታት በላይ ይፈጃል፤ ሆኖም ግን እንደቪክቶሪያ ሀይቅ መቆጣጠር የሚቻልበት መንገድ አለ፡፡ የፌደራልና የክልሉ መንግሥት ከጎረቤት አገሮች ልምድ በመቅሰም ተግባራዊ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ በውጭ አገርና በአገር ውስጥ የተቋቋሙ ማኅበራት ባለቤቱ የሆነውን ሕዝብ ከማዘናጋት በስተቀር የፈየዱት የለም፡፡

3) ለትልልቅ ከተሞች ዘመናዊ የቆሻሻ ማስወገጃ ሥርዓት መገንባት ያስፈልጋል፡፡
ቆሻሻን ማኔጅ ሩዋንዳ ለአፍሪካውያን ሁሉ ሞዴል መሆን የምትችል አገር ነች፡፡ የኪጋሊ ከተማ ንፅህና ከአውሮፓ ከተሞች ሁሉ የሚወዳደር ነው፡፡ ቆሻሻ አወጋገድና ተፈጥሮን አጠቃቀም የሩዋንዳን ሞዴል መከተል ያስፈልጋል፡፡ የባህር ዳርና የጎንደር ከተሞች የሚደፉ ቆሻሻዎች ላይ ሳይውል ሳያድር መፍትሄ መፈለግ ያስፈልጋል፡፡

በተጨማሪም ቆሻሻቸውን ወደ ሀይቁ የሚደፉ የባህር ዳር ከተማ ተቋማትን ጥብቅ ፍተሻ በማድረግ መቆጣጠር ያስፈልጋል፡፡ ወደ ሀይቁ ቆሻሻውን የሚልክ ተቋምን ለጠቆመ ሽልማት ቢዘጋጅ እርስ በእርስ መጠቋቆም ስለሚኖር ኅብረተሰቡ ሀይቁን ሊጠብቀው ይችላል፡፡

Check Also

AMHARA FANO in London at Ethiopian Embassy

የዲያስፓራ መንገደኞች የሚያጋጥማቸው መከራ!

በቦሌ አየር ማረፊያ በፍተሻ እና ጥበቃ አካላት ተጓዦች ላይ የሚፈፀም ውንብድና እና ዝርፊያ! ድርጊቱ የተፈፀመው …

Multi threaded Redundant Dedicated Server in USA and in Europe.