Breaking News
Home / Amharic / የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቁጠባ ቤቶች ልማት ዕግድ የተጣለባቸውን የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ለይቶ እንዲያሳውቅ በፍርድ ቤት ታዘዘ፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቁጠባ ቤቶች ልማት ዕግድ የተጣለባቸውን የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ለይቶ እንዲያሳውቅ በፍርድ ቤት ታዘዘ፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቁጠባ ቤቶች ልማት ኢንተርፕራይዝ፣ ዕግድ የተጣለባቸውን የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ለይቶ እንዲያሳውቅ በፍርድ ቤት ታዘዘ፡፡

ትዕዛዙን የሰጠው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ስምንተኛ ፍትሐ ብሔር ችሎት ነው፡፡ ኢንተርፕራይዙ ባለሦስት፣ ባለሁለትና ባለአንድ መኝታ የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች በየትኞቹ ሳይትና ብሎክ እንደሚገኙና የተሰጣቸውን የቤት ቁጥር ጭምር ለይቶ እንዲያሳውቅ ተነግሮታል፡፡ ኢንተርፕራይዙ ትዕዛዙን ፈጽሞ የሚቀርበው ሐሙስ ሐምሌ 18 ቀን 2011 ዓ.ም. ነው፡፡

የ40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕግድ የተጣለባቸው በምዝገባ ወቅት መቶ በመቶ ክፍያ የፈጸሙ በርካታ ተመዝጋቢዎች ቅድሚያ የዕድሉ ባለቤቶች እንደሚሆኑ ተነግሯቸው ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር ውል ከፈጸሙ በኋላ፣ የካቲት 27 ቀን 2011 ዓ.ም. የከተማ አስተዳደሩ ከ18 ሺሕ በላይ የሚሆኑ 40/60 የጋራ መኖሪያ ቤቶችን፣ ከ40 በመቶ በላይ የቆጠቡ ሁሉ በዕጣው በማካተቱና በማውጣቱ ምክንያት ክስ በመመሥረቱ መሆኑ ይታወሳል፡፡

ፍርድ ቤቱ መጀመርያ ክስ ባቀረቡት 98 ሰዎች አቤቱታ መሠረት ሁሉንም ዕጣ የወጣባቸውን የጋራ መኖሪያ ቤቶችና በቀጣይ የሚወጡትም ጭምር ዕግድ የጣለ ቢሆንም፣ ቆይቶ ክስ ባቀረቡት ልክ ብቻ በማገድ የሌሎችን ቤቶች ዕግድ ማንሳቱ ይታወሳል፡፡ በአሁኑ ጊዜ መቶ በመቶ መክፈላቸውን በመግለጽ ለፍርድ ቤት ክስ ያቀረቡ ተመዝጋቢዎች ቁጥር 700 መድረሱ እየተነገረ ነው፡፡

 

የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ለማስተላለፍ የወጣው መመርያ  የሕገ መንግሥቱን መርሆዎች እንደሚቃረን ተገለጸ

መመርያው ለትርጉም ወደ ፌዴሬሽን ምክር ቤት ተላከ

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ለተጠቃሚዎችና ለልማት ተነሺዎች ለማስተላለፍ ያወጣው መመርያ ቁጥር 1/2008 አንቀጽ 44 (ሐ እና ሠ)፣ የሕገ መንግሥቱን አንቀጽ (40) እና ሌሎች መርሆችን የሚቃረን መሆኑ ተገለጸ፡፡

መመርያው የሕገ መንግሥቱን ድንጋጌና መርሆች እንደሚቃረን የገለጸው የሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ ሲሆን፣ መመርያውንና የሕገ መንግሥቱ ተቃርኖዎች በመለየት ውሳኔ እንዲሰጥበት ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ልኳል፡፡

አጣሪ ጉባዔው ተቃርኖውን ለማጥናትና ለማረጋገጥ የቻለው፣ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት በመዝገብ ቁጥር 150818 ሰኔ 28 ቀን 2010 ዓ.ም.፣ በአንድ አመልካችና በከተማ አስተዳደሩ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ኤጀንሲ መካከል፣ ሲካሄድ የነበረን ክርክር ሲመረምር ከቆየ በኋላ ውሳኔ ከመስጠቱ በፊት፣ ተፈጻሚነት ያለውን መመርያ ቁጥር 1/2008 እና የሕገ መንግሥቱን አንቀጽ 44 ጉባዔው መርምሮ እንዲያሳውቅ ከላከለት በኋላ መሆኑን፣ ጉባዔው ለምክር ቤቱ የላከው ውሳኔ ይገልጻል፡፡

ጉባዔው የጉዳዩን ሕገ መንግሥታዊነት በመረመረበት ወቅት የጉዳዩን ክብደት በመረዳቱ፣ የከተማው አስተዳደር ቤቶች ልማት ኤጀንሲ ኃላፊንና ባለሙያ አስቀርቦ በጉዳዩና በድንጋጌዎቹ ዙሪያ ተጨማሪ ማብራሪያ መቀበሉን አስታውቋል፡፡

መመርያ ቁጥር 1/2008 አንቀጽ 44 ላይ፣ ‹‹የቤት ዕድለኛ በሞተ ጊዜ ዕድሜያቸው 18 ዓመት የሞላቸው የሟች ልጆች በሟች ስም የወጣውን ዕጣ አይወርሱም፤›› በማለት መደንገጉን ጉባዔው አስታውሷል፡፡

ይኼ ደግሞ በወራሾች መካከል ልዩነት በመፍጠር ቤት የሌላቸው ግለሰቦች፣ በውርስ መልክ የሚያገኙትን መብት የሚያጣብብና ከሌሎች የሕገ መንግሥቱ መርሆች ጋር የሚጋጭ ሆኖ እንዳገኘው በዝርዝር አስረድቷል፡፡

በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 40 ሥር የተደነገገውን የዜጎችን የንብረት መብት የሚያጣብብ፣ ከሌሎች የሕገ መንግሥት መርሆዎች ጋርም ይጋጫል ብሏል፡፡ በመሆኑም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ለተጠቃሚዎች ለማስተላለፍ የወጣው መመርያ 1/2008 አንቀጽ 44 (ሐ እና ሠ) ከሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 40 እና ከሌሎች የሕገ መንግሥቱ መርሆዎች ጋር ስለሚቃረን፣ የሕገ መንግሥት ትርጉም እንዲሰጥበት ጉዳዩን ለፌዴሬሽን ምክር ቤት መላኩን አስታውቋል፡፡

የሕገ መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 82 ድንጋጌ መሠረት ተቋቁሞ ሕገ መንግሥታዊ መብት እንዲከበር የሚሠራ ተቋም መሆኑ ይታወቃል፡፡ 

Check Also

ከጎጃም አማራ ፋኖ የተሰጠ መግለጫ – ዘመነ ካሴ – Amhara FANO Gojjam

የትግራይ ምሁር የወያኔና የአቢይ አህመድን ሴራ አጋለጠ።

News in Pictures

Time in Ethiopia

Multi threaded Redundant Dedicated Server in USA and in Europe.