Breaking News
Home / Amharic / ከአማራ ፋኖ በባህርዳር የተሰጠ መግለጫ !

ከአማራ ፋኖ በባህርዳር የተሰጠ መግለጫ !

ከአማራ ፋኖ በባህርዳር የተሰጠ መግለጫ

 

እንደሚታወቀዉ የአማራ ህዝብ ማህበራዊ እረፍቱን ማጣት ከጀመረ በርካታ ዓመታት ተቆጥሯል ፤ባለፉት ሶስት አመታት ግን መንግስት መር ጭፍጨፋዎች፤ ግድያዎችና ዉድመቶች በአማራ ህዝብ ላይ በሰፊዉ ተባብሰዉ ቀጥለዋል፡፡ በመሆኑም ባለፉት ሶስት ዓመታት ብቻ ሚሊዮን አማራዎች ለስደት፣ ረሃብና መፈናቀል ሲጋለጡ፤ በመቶ ሺ የሚቆጠሩ የአማራ ተወላጆች ደግሞ መንግስት መር በሆነ የዘር ጭፍጨፋ እንዲያልቁ ተደርገዋል፡፡ በእንቅርት ላይ ጀሮ ደግፍ እንዲሉ ደግሞ ሰሜን ክፍሉን ‹የተራዘመ ጦርነት ዉስጥ እንዲከርም› በማድረግ የአማራ ህዝብ በቁጥር ለመግለፅ በሚያስቸግር አሃዝ ብዙ ንብረት ሲወድምበት፤ ሃብትና ንብረቱን ከማጣትም በላይ ዉድ ልጆችን ሲሰዋ ከርሟል፡፡

ፋኖ የአማራ ህዝብ እንደ ህዝብ የህልዉና አጣብቂኝ ዉስጥ ሲገባ፤ እንደ ክልል ደግሞ የመፈራረስ እድል ሲገጥመዉ ስንቁን ከቤቱ ትጥቁን ከአያቱ ይዞ በመዝመት የአማራ ህዝብን አለኝታነት ያረጋገጠ ባህላዊ ሰራዊት ነዉ፡፡ ይህ ሃይል በደህና ጊዜ አራሽ፤ በችግር ጊዜ ደግሞ ፈጥኖ ደራሽ ትዉፊቱን ሲያስቀጥል በተለያዩ አዉደ ዉጊያዎችና ምሽግ ሰበራዎች በመሳተፍ ጭምር እንጅ ጭንቅ ቀን ሲመጣ ሀብት መዝብሮ የሚሮጥ ስብስብ አልነበረም፡፡

የአማራ ፋኖ በባህርዳር በአርቢት-ጋሸና ግንባር ቀጥተኛ ተሳትፎ በማድረግ እስከሞት ድረስ በታመኑ የህዝብ ልጆች ላይ ማለትም ‹‹ፋኖ ጌታቸዉ ሙጩ›› እና ‹‹ፋኖ ሰለሞን አባተ›› ላይ የእስራት ሁኔታ ሲገጥማቸዉ በሌሎች በርካታ አባላቶቹ ላይ ደግሞ የወከባ፤ ሽብርና ከበባ ሁኔታን እያስተናገዱ ይገኛሉ፡፡ በመሆኑም የአማራ ፋኖ በባህርዳር በወከባ፤ እስር፤ ከበባና እንግልት ዉስጥ ሁኖም ከዚህ በታች ያሉትን አቋም ለአካባቢያችን፤ አማራና ብሎም የኢትዮጵያ ህዝብ ለማሳወቅ ይገደዳል፡፡

1ኛ). ከበጌምድር ወንድሞቻችን ‹የወልቃይት አስመላሽ ኮሚቴ› የተላከልንን የዝግጅት ትዕዛዝ ለማስተጎጎል የተሸረበ ሴራ መሆኑን ስለምንረዳ እኛ ላይ እየተደረገ ያለዉ ደም አፋሳሽ ሂደት በአስቸኳይ ወደ ሰገባዉ እንዲመለስ ስንል ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡

2ኛ). ነገሮቹን የምናይበት የትዕግስት መነፅር እንደ ፍርሃት የሚቆጠር ሁኖ ራስን ወደመከላከል አጠፋ ስንገባ የአማራ ክልል ርዕሰ መዲናዋ ባህርዳር ለሚፈጠርባት ትርምስ፤ ሁከትና ብጥብጥ ‹መንግስትና መንግስት መሩ የአፈና ቡድን› ሃላፊነቱን ይወስዳል፡፡

3ኛ). የሐይማኖት አባቶች፤ የሃገር ሽማግሌዎችና ወጣቶች ነገ ይህ ለምን ተፈጠረ ብሎ ሙሾ አዉራጅነትና የሚዲያ ጋጋታን ከማስከተላቹህ በፊት ‹መንግስትንና መንግሰት መሩ የአፈና ቡድኑን› ተዉ ብላቹህ ትገስፁ ዘንድ እናሳስባለን፡፡

4ኛ). ፋኖ ላይ የሚደረጉ መጠነሰፊ እንግልቶች ባሉበት ሳይገቱ ከቀጠሉና የታሰሩብን አባሎቻችን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ የማይፈቱ ከሆነ ፋኖ ለሚዎስደዉ የአመፅ፤ ሰልፍ፤ ህዝባዊ እምቢተኝነትና አድማ (እንደ አስፈላጊነቱ እያደገ የሚሄድ) እንቅስቃሴዎች መንግስት ሃላፊነቱን ሙሉ ለሙሉ ይወስዳል፡፡

5ኛ). የአማራ ፋኖ በባህርዳር የአማራ ክልል ዋና ከተማ ላይ እንደመቀመጡ መጠን ለዘርፈ ብዙ ጥቃትና እንግልት ተጋላጭ በመሆናችን ራሳችንን ለመከላከል በምናደርገዉ ተጋድሎ በሁሉም አካባቢ ማለትም በአማራ ነባር አፅመ ርስቶች ሸዋ፤ ወሎ፤ ጎንደርና ጎጃም ያሉ የፋኖ አደረጃጀቶች እዉቅናዉ እንዲኖራቹህና ከአያቶቻችን በወረስነዉ የመተጋገዝ መንፈስ እንድነታችንን እንድናጠናክር ስንል ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡

አርበኝነት ዉርሳችን ሲሆን ታሪካዊነት ደግሞ ትርፋችን ነዉ!!!

ግንቦት 09/2014

Check Also

ሰሎሞን ካሳ ማነው? Who is Solomon Kassa?

አንከር ሚዲያ እንደዘገበው .. ለማታውቁት ሰለሞን ካሳ ይባላል ., ወንጀለኛው የሆነው ይህ ሰው የህዝብ ድምፅ …

የአድዋ በአል በለንደን ከተማ በደማቅ ተከበረ

Multi threaded Redundant Dedicated Server in USA and in Europe.