Breaking News
Home / Amharic / ህገ መንግስቱ እንዲቀየር ጥረት እንደሚያደርግ አብን አስታወቀ!

ህገ መንግስቱ እንዲቀየር ጥረት እንደሚያደርግ አብን አስታወቀ!

ባሕር ዳር፡ ግንቦት 17/2011ዓ.ም (አብመድ) የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ (አብን) ከጎንደር ከተማ ወጣቶች እና ነዋሪዎች ጋር ዛሬ ተወያይቷል። ተወያዮቹ አብን ቢያተኩርባቸው ይጠቅማሉ ያሏቸውን ሀሳቦች አንስተዋል።

አብን ለአማራ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያ ትንሳኤ መስራት አለበት፤ እኛ ሁልጊዜ እሳት ማጥፋት የለብንም፤ ይልቁንም ችግር ከመከሰቱ በፊት መከላከሉ ላይ መሰራት አለበት ብለዋል። ለአማራ የመኖር መብት፣ የኢኮኖሚ እና የማንነት ጥያቄዎች ትኩረት ሰጥቶ እንዲታገልም ሀሳብ ሰጥተዋል።

በኃይማኖት ለማጋጨት የሚሰሩ ሀይሎች መበራከታቸውን የተናገሩት ተወያዮቹ አብን እነዚህ ችግሮች እንዲቀረፉ ከሰራ ለኢትዮጵያ ትልቅ ተስፋ እንደሚሆን ያላቸውን እምነት ገልፀዋል።

ዘራፊዎችን እና ሙሰኞችን እንዲታገል፣ በጤናው ዘርፍ ማሻሻያ እንዲደረግ እና በነበረው ስርዓት በኢትዮጵያ ላይ ግፍ የሰሩ ግለሰቦች ለህግ እንዲቀርቡ አብን መስራት አለበት የሚሉ ሃሳቦችንም አቅርበዋል።

የንቅናቄው የስትራቴጂክ ጥናት ኃላፊ አቶ የሱፍ ኢብራሂም ለተወያዮቹ በሰጡት ማብራሪያ የኢትዮጵያ ህገ መንግስት አማራን ያገለለ በመሆኑ እንዲቀየር አብን ጥረት ያደርጋል፤ የራሱንም አማራጭ ያስቀምጣል ብለዋል። የአማራ ይዞታዎች የሚመለሱበትን መንገድ የሚያሳይ ሠነድ ንቅናቄው አጠናቅሮ ማስቀመጡንና የወልቃይት ጉዳይ የወልቃይት ብቻ ሳይሆን የመላው አማራ ሕዝብ ጉዳይ መሆኑን ነው ያስገነዘቡት።

የክልሉ ሕዝብ ማንኛውም ጥያቄ በአስቸኳይ እንዲመለስ እንፈልጋለን፤ ለተግባራዊነቱም እንሰራለን ያሉት አቶ የሱፍ ለውጡ የአማራን ሕዝብ ጥቅም ያስከበረ መሆን እንዳለበት፣ በአንድነት በመደራጀትም የጋራ ጥቅምን ማረጋገጥ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

አብን ሁሉም ሕዝብ እኩል ተጠቃሚ እንዲሆን በዘላቂነት የሚሰራ ፓርቲ መሆኑንና በአንድነት ተደራጅቶ ሀገር የማትፈርስበትን ታላቅ ስራ መስራት እንደሚገባም አቶ የሱፍ ተናግረዋል።

የአብን የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ መልካሙ ሹምዬ በበኩላቸው ሁሉም ሰው በያለበት ዘርፍ ተደራጅቶ ሕዝቡን መጥቀም መቻል እንዳለበት ነው የተናገሩት። አብን በሰላማዊ መንገድ ሥልጣን ተረክቦ የኢትዮጵያን ትንሳኤ ለማረጋገጥ የሚሰራ የፖለቲካ ፓርቲ ስለመሆኑም አብራርተዋል። ክልሉ ጠንካራ እና በስነ ምግባር የታነፀ የፀጥታ ኃይል እንዲኖረው ንቅናቄው ትግል ማድረጉን፤ አሁንም መልካም ስራ እንዲሰራ ግፊት እንደሚያደርግ አቶ መልካሙ አስረድተዋል።

የህግ ባለሙያ እና የሰብዓዊ መብት ተሟጋቹ አቶ ውብሸት ሙላት የአባቶችን ታሪክ በማስቀጠል እና አዲስ ስራ በመስራት ወጣቱ ትውልድ ለሀገር ግንባታ እንዲተጋ ጠይቀዋል። ጨቋኙን ስርዓት ከማስወገድ ባሻገር ለሕዝብ ጥቅም እና እኩልነት መስራት እንደሚገባም ነው የተናገሩት።

“ሁላችንም በኢኮኖሚውም መደራጀት መቻል አለብን፤ በኢኮኖሚ ካልተደራጀን ሀገራችንን እንደ ሀገር ማስቀጠል አይቻልም፤ ፖለቲካውን ብቻ ማራገብ ለሕዝባችን አይጠቅምም” በማለት አሳስበዋል። ክልሉን ለመከፋፈል የሚሰሩ ግለሰቦች መኖራቸውን ተገንዝቦ ለመፍትሔው በጋራ መስራት እንደሚጠቅምም አቶ ውብሸት አስገንዝበዋል።

ዘጋቢ:- ታርቆ ክንዴ – ከጎንደር

Check Also

AMHARA FANO in London at Ethiopian Embassy

የዲያስፓራ መንገደኞች የሚያጋጥማቸው መከራ!

በቦሌ አየር ማረፊያ በፍተሻ እና ጥበቃ አካላት ተጓዦች ላይ የሚፈፀም ውንብድና እና ዝርፊያ! ድርጊቱ የተፈፀመው …

Multi threaded Redundant Dedicated Server in USA and in Europe.